20111230

የቅዱሳን መላእክት አማላጅነት ክፍል 2

በክፍል አንድ ትምህርታችን መቆም የሚለው ቃል ማማለድ የሚል ፍቺ ይዞ የሚገኝበትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል አይተን ነበር፡፡ አያይዘንም የመላእክትን አማላጅነት ከዚሁ ቃል አንጻር ተረድተናል፡፡ በክፍል ሁለት ትምህርታችን ደግሞ ማየት ከሚለው ቃል አንጻር የመላእክትን አማላጅነት እንማራለን፡፡

መቆም እንደሚለው ቃል ሁሉ ‹‹ማየት›› የሚለው ቃልም በመጽሐፍ ቅዱስ የራሱ የሆነ አገባባዊ ፍቺ አለው፡፡ በዓይን መለማመጥ፣ ማሳዘን፣ መቆጣት፣ ተስፋ ማድረግ እና ማስፈራራት ይቻላል፡፡ ‹‹የሁሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል፡፡›› እንዲል፡፡ (መዝ 144.15) ስለዚህ ‹‹ማየት›› መመርመር ወይም ንስሐ መግባት፣ መለመን፣ መጸለይ፣ ተስፋ ማድረግ፣ ማማለድ፣ መስማት፣ መቀበል፣ መቆጣት ወዘተ የሚሉ ፍቺዎች አሉት፡፡

ማየት የሚለው ቃል ከ እግዚአብሔር አንጻር

በተለይ ከእግዚአብሔር አንጻር ካየነው ማየት የሚለው ቃል መስማት፣ መቀበል፣ ይቅር ማለት የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ "እግዚአብሔር እገሌን በዓይነ ምሕረት አየው" ማለት አሰበው፣ ጎበኘው፣ ማረው፣ ሰማው ፣ ይቅር አለው ማለት ይሆናል፡፡ እንደ አገባቡ ተቆጣው ማለትም ሊሆን ይችላል፡፡ ለጠቀስናቸው ሐሳቦች ከመጽሐፍ ቅዱስ ‹‹እግዚአብሔርም ወደ አቤልና ወደ መሥዋዕቱ ተመለከተ፡፡››፤ ‹‹እነሆ የእግዚአብሔር ዓይኖች ወደሚፈሩት ናቸው፡፡››፤ ‹‹የእግዚአብሔር ዓይኖች ወደ ጻድቃን ጆሮውም ወደ ጩኸታቸው ነው፡፡›› የሚሉትን ማስረጃዎች መመልከት ብቻ እንኳን ይበቃል፡፡ (ዘፍ 4।4፤ መዝ 32।18፤ 33।15)

ከፍጥረት አንጻር

"ማየት" የሚለውን ቃል ከሰው አንጻር ወይም ከፍጥረት ሁሉ አንጻር ካየነው ደግሞ ሌሎች ፍቺዎች ይኖሩታል፡፡ ‹‹አቤቱ አምላኬ እየኝ ስማኝም፡፡›› ሲል ማረኝ ለማለት ነው፡፡ "ማየት" መመርመር ሲሆን ‹‹ራስህን ለካህን አሳይ›› ይላል፡፡ ይህ ደግሞ ራስህን አስመርምር፣ ንስሐ ግባ ማለት ነው፡፡ (ማቴ8.4፤ መዝ12.3) በእንግሊዝኛውም ይህን የመሰለ ነገር አለ፡፡ ነጮቹ ሕክምና ላድርግ ወይም ልመርመር ለማለት ‹‹ሐኪሜን ልይ›› ይላሉ፡፡

ከላይ በተጠቀሰው መልኩ ‹‹ማየት›› የሚለውን ቃል ትርጉም በትክክል በመረዳት የመላእክትን አማላጅነት በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል፡፡

ለሰው ልጆች በሙሉ ለየራሳቸው ጠባቂ መላእክት አሏቸው፡፡ ይህንንም ያደረገው ፈጣሪ ነው፡፡ ‹‹መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና›› የሚለው የነቢዩ የዳዊት መዝሙር ፈጣሪ ለሰው ልጆች የሚጠብቋቸው መላእክትን እንዳዘጋጀ ያስረዳል፡፡ (መዝ90.11) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌያዊ ትምህርቱ ለበለሱ አትክልተኛ መቅጠሩ በበለስ ለተመሰሉ የሰው ልጆች ለእያንዳንዳቸው ጠባቂና ተንከባካቢ መልአክ ማዘጋጀቱን የሚያስረዳ ነው፡፡ (ሉቃ13.6-9) በትንቢተ ዳንኤል መጽሐፍ ውስጥ መልአኩ ‹‹ቅዱስ ጠባቂ›› የተባለው በዚህ ምክንያት ነው፡፡ (ዳን4.13፤ 4.23) በተጨማሪም ለሰው ልጆች ሁሉ ጠባቂ መልአክ እንዳላቸው በወንጌል ‹‹መላእክቶቻቸው›› በሚል የተቀመጠው ቃል ብቻ ምስክር ነው፡፡ (ማቴ18.10)

መላእክት እንደ ታላላቅ ወንድሞቻችን የምንቆጥራቸው እነርሱም ደግሞ እኛን እንደ ታናናሽ ወንድሞቻቸውና እኅቶቻቸው የሚያዩን ቤተሰቦቻችን ናቸው፡፡ እነርሱ ከእኛ በፊት በዕለተ እሑድ የተፈጠሩ የአምላክ ልጆች ሲሆኑ እኛ ደግሞ በዕለተ ዐርብ የተፈጠርን የእግዚአብሐር ልጆች ነንና፡፡ (ኢዮ1.6፤ 2.1፤ ዮሐ1.12) የአንድ አባት ልጆች ደግሞ ወንድሜ እኅቴ እንደሚባባሉ የታመነ ነው፡፡ ስለዚህ መላእክት እየሳሱ ይጠብቁናልና እኛ የእነርሱ ገንዘብ ነን፡፡ እነርሱም የእኛ ገንዘቦች በመሆናቸው ‹‹መላእክቶቻቸው›› ተብለዋል፡፡ ይህም ከወንጌሉ ትረካ የምናታገነው ነው እንጂ በብልሃት የተፈጠረ ቃል አይደለም፡፡

እነዚህ ጠባቂ መላእክት ስለ ሰው ልጅ የእግዚአብሔርን ፊት እንደሚያዩ ወንጌል ይናገራል፡፡ ‹‹መላእክቶቻቸው ዘወትር በሰማያት ያለውን የአባቴን ፊት ያያሉና›› እንዲል፡፡ (ማቴ18.10) ይህም ዐረፍተ ነገር ያለ ምንም ጥርጥር የመላእክትን አማላጅነት የሚያሳይ ነው፡፡ ማየት መጸለይ ማማለድ የሚል ትርጉም እንዳለው ቀደም ሲል በሚገባ ተቀምጧልና፡፡ ካልሆነ ግን በምን ሊተረጎም ይችላል? የጥቅሱን ሙሉ ሐሳብ ስንወስድ ሰዎችን አትናቁ! የምትንቋቸውን ሰዎች የሚጠብቁ መላእክት ዘወትር የአባቴን ፊት ያያሉ የሚል ነው፡፡ ይህም ለተናቁት ሰዎች ለምነው ያማልዷቸዋል፡፡ የምትንቁትን እናንተን ደግሞ ጸልየው ያስፈርዱባችኋል የሚል ማስጠንቀቀቂያ ቃል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

ለማጠቃለል በቃል የሚጠና ሐሳብና ጥቅስ

ጽንሰ ሐሳብ፡- "ማየት" መጸለይ፣ ማማለድ፣ መስማት፣ መቀበል፣ ይቅርታ ማድረግ ማለት ይሆናል፡፡ እንዲህ ከሆነ መላእክት ስለ እኛ የፈጣሪን ፊት ያያሉ ማለት ያማልዳሉ ማለት ነው፡፡

በቃል የሚጠኑ ጥቅሶች

1ኛ. "ማየት" መስማት፣ መቀበል ሲሆን በፈጣሪ አንጻር

(ዘፍ4.4፤ መዝ32.18፤ 33.15)

2ኛ."ማየት" መጸለይ፣ ማማለድና ይቅርታ መጠየቅ ሲሆን ከፍጡር አንጻር

(ማቴ18.10፤ ማቴ8.4፤ መዝ12.3)

ይቀጥላል

3 comments:

  1. melaketoche lyamaledu ayechelum amalajachen kerstose eyesuse new melaket ena kedusane seweche yemyamaledu biohen noro kerstose wedezhe alem memetate balasefelgew neber neger gen wede gezyanher yemimalede setefa egzya bher andeya lejune yemiwedwen wedzhe aleme lekotale selzhe yekerstose eyesusene amalagente alemkebele kerstosen mekade new

    ReplyDelete
  2. geta yekr yebelesh.
    endat amelak amalaje yehonal?
    eyesus wedezeh meder yemtaw aliyam yeteweledw le adam begebalet kale meseret new.
    eyesus manew bemel eries yetesbekwen sbeket kelebsh admtshw ezhu website liy tagejewalsh.geta mastewalen yestan.

    ReplyDelete