20111231

የመላእክት አማላጅነት - ክፍል ሦስት

በክፍል አንድና በክፍል ሁለት ትምህርታችን የመላእክትን አማላጅነት በተለያየ መንገድ ተመልክተናል፡፡ እነዚያን ያላነበባችሁ በፌስቡክ ኖት ውስጥ ያኖርኩአቸው በመሆኑ ያንን በመክፈት ማንበብ እንደምትችሉ ለመጠቆም እወዳለሁ!
ሦስተኛውን ክፍል እነሆ፡-

‹‹አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ›› ያለው የትንቢት ቃል ይፈጸም ዘንድ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው በምሳሌ አስተምሯል፡፡ /መዝ77.2/ በምሳሌ ካስተማራቸው ትምህርቶች መካከል አንዱ የመላእክትን አማላጅነት የሚያሳይ ነው፡፡
ሙሉ የወንጌሉ ቃል ከዚህ ቀጥሎ የምናነበው ሲሆን ነጥቦቹን አንድ በአንድ እንመለከታለን፡፡

“ይህንም ምሳሌ አለ። ለአንድ ሰው በወይኑ አትክልት የተተከለች በለስ ነበረችው፥ ፍሬም ሊፈልግባት መጥቶ ምንም አላገኘም። የወይን አትክልት ሠራተኛውንም። እነሆ፥ ከዚህች በለስ ፍሬ ልፈልግ ሦስት ዓመት እየመጣሁ ምንም አላገኘሁም፤ ቍረጣት፤ ስለ ምን ደግሞ መሬቱን ታጐሳቍላለች? አለው። እርሱ ግን መልሶ፦ ጌታ ሆይ፥ ዙሪያዋን እስክኰተኵትላትና ፋንድያ እስካፈስላት ድረስ በዚች ዓመት ደግሞ ተዋት።ወደ ፊትም ብታፈራ፥ ደኅና ነው፤ ያለዚያ ግን ትቈርጣታለህ አለው።” /ሉቃ13।6-9/

ይህን ቃል ጽፎ ያቆየልን ሐዋርያ ቅዱስ ሉቃስ ቢሆንም ትምህርቱን ያስተማረው ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ‹‹ይህንም ምሳሌ አለ›› ብሎ ታሪኩን በመጀመሩ ትምህርቱ ምሳሌያዊ መሆኑን ለመረዳት አያስቸግርም፡፡
የበለሲቱ ጌታ /ባለቤት/ ከአንድም ሁለት ሦስት ጊዜ ተመላልሶ ፍሬ ቢፈልግባት ምንም ስላላገኘባት እንድትቆረጥ ለሠራተኛው ጥብቅ ትእዛዝ ሰጠ፡፡ በዚህ ጊዜ ሠራተኛው በፍጥነት ሊቆርጣት ይችል ነበር፡፡ ያን ቢያደርግም በጌታው ዘንድ ሊመሰገን ይችላል፡፡ ምክንያቱም የታዘዘውን አድርጓልና፡፡

ነገር ግን ጌታውን ‹‹በዚች ዓመት ደግሞ ተዋት›› በማለት ስለ በለሲቱ ለመነላት፡፡ አማለዳት ማለት ነው፡፡ ለሌላ ወገን የሚደረግ ልመና ምልጃ ነውና፡፡ የሚገርመው ደግሞ በለሲቱ እንዲለምንላት አልተማጸነችም፡፡ ሠራተኛው በራሱ ደግነት በፈቃዱ ተነሣስቶ ለመነላት እንጂ፡፡ ብትለምነው ደግሞ የበለጠ ሊያደርግ እንደሚችል መረዳት አያዳግትም፡፡ ሊያማልድ ያልተዘጋጀ ወይም ያላሰብ ሰው እንኳን እባክህ አማልደን ብለው ሲልኩት እምቢ እንደማይል ሁሉ ይህ ሠራተኛ ቢለመን የበለጠ ሊያደርግ መቻሉ እሙን ነው፡፡

የበለሲቱም ጌታ የቀጠርኩህ እንድትታዘዘኝ እንጂ እንድትለምነኝ አይደለም ሳይል የሠራተኛውን ምልጃ ተቀበለ፡፡ ይህም ምልጃ ተቀባይ ጌታ መሆኑን ያሳያል፡፡

ምሳሌው እንዴት እንደሚተረጎም እንመልከት፡- የበለሷ ጌታ /ባለቤት/ ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው፡፡ በለሲቱ ደግሞ እስራእላውያንን ቀጥሎም የሰውን ዘር በሙሉ ያመለክታል፡፡ ሠራተኛ የተባለውም ሰውን የሚጠብቅ መልአክ /ዑቃቢ መልአክ/ ነው፡፡ ከበለሲቱ በተስፋ የተጠበቀው ፍሬ ደግሞ ከሰው ዘር በሙሉ ፈጣሪ የሚፈልገው የቀና ሃይማኖትና መልካም ምግባርን ነው፡፡ ሦስት ጊዜ ተመላልሶ ፍሬ ማጣቱ ፈጣሪ በታዳጊነት፣ በወጣትነትና በጎልማስነት ጊዜ ሁሉ ፍሬ እንደሚፈልግብን ያሳያል፡፡ ‹‹ቁረጣት›› ማለቱ ፍሬ ሲያጣብን ያለ ዕድሜም መቀሠፍ እንዳለና ሞት እንደሚፈረድብን ያሳያል፡፡ በአጠቃላይ ይህ ሠራተኛ ለበለሲቱ እንደለመነላት መላእክትም ለእኛ እንደሚለምኑልን እንደሚያማልዱን ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን መመልከት አለብን፡፡ ይህን ካልተቀበልን ምን ብለን ልንተረጉመው ነው? ‹‹ቅዱስ ጠባቂ›› የሚባል መልአክ መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ /ዳን4।13፤4।23/ እንዲጠብቁንም ያዘዛቸው ፈጣሪ ነው፡፡ ‹‹መላእክቱን ስለ አንተ ያዛቸዋል፡፡›› ተብሏልና፡፡ /መዝ90।11/

ይህ ምሳሌያዊ ትምህርት በርካታ መልእክቶችን ሊያስተላልፍ ይችላል፡፡ እያንዳንዱ ቃልና ዐረፍተ ነገርም ብዙ ምሥጢር ይዟል፡፡ የእኛ ርእስ ግን ስለ ምልጃ ስለሆነ በዚህ እንወሰናለን፡፡ ይሁን እንጂ ጎላ ያለ ጥያቄ መልሶ ለማለፍ ያህል አንድ ሰው የበለሲቱ ባለቤት ‹‹ትቆረጥ›› ሲል ሠራተኛው ደግሞ ‹‹በዚች ዓመት ደግሞ ተዋት›› ማለቱ ለበለሲቱ ከባለቤቱ ይልቅ ሠራተኛው ያዘነላት አያስመስልም? ሊል ይችላል፡፡
ለበለሲቱ ከሠራተኛው ይልቅ ያዘነላት ጌታዋ ነው እንጂ ሠራተኛው አይደለም፡፡ እንዴት ቢባል ጌታዋ ከአንድም ሦስት ጊዜ ሳይቆርጣት አልፎአታል፡፡ በተጨማሪም ሠራተኛው የለመነላት ለአንድ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እንዲያው ከዚያ በኋላ ካላፈራች ‹‹ትቆርጣታለህ›› ሲል ተናገረ፡፡ ጌታዋ ለሦስት ጊዜ የታገሣትን እርሱ ግን አንዴ ከለመነላት በኋላ ብትቆረጥም ቅር እንደማይለው አስረዳ፡፡ ታዲያ ከጌታዋ ይልቅ እርሱ ራራ ለማለት እንዴት ይቻላል? በዚያውም ላይ ያ ሠራተኛ ቢለምንላትም ይቅር ያላት ግን ጌታዋ መሆኑን መርሳት አይገባም፡፡ ከዚህ ሁሉ ጋር እንዲህ አዝኖ የሚያማልዳትን ሠራተኛ ያዘዘላት እኮ ጌታዋ ነው፡፡ በመጨረሻ ትምህርቱ ምሳሌያዊ ነው፡፡ ‹‹ቁረጣት›› ያለው ጌታዋ የፈጣሪ ምሳሌ እንደመሆኑ መጠን ሠራተኛው የሚያቀርብለትን የምልጃ ጥያቄ አስቀድሞ ያውቃልና በለሲቱ እንደማትቆረጥ ያውቅ ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ እርሱ በበለሲቷ ላይ ያለውን የማዘዝ ሙሉ ሥልጣን እና የሠራተኛውን ማለትም የጠባቂ መልአኩን የማማለድ ሥራ ሊያሳይ በሚችል መንገድ ምሳሌውን እርሱ ባወቀ መስሎ ተናገረ፡፡

-በቃል የሚጠና ጥቅስ ሉቃ 13।6-9
-ሐሳብ - የበለሲቷ ምሳሌ
-ትምህርት - በሠራተኛው ልመና አንጻር የመላእክትን አማላጅነት ማሳየት

ይቆየን!

የቅዱሳን መላእክት አማላጅነትና ተራዳኢነት የፈጣሪ ቸርነት አይለየን!



20111230

የቅዱሳን መላእክት አማላጅነት ክፍል 2

በክፍል አንድ ትምህርታችን መቆም የሚለው ቃል ማማለድ የሚል ፍቺ ይዞ የሚገኝበትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል አይተን ነበር፡፡ አያይዘንም የመላእክትን አማላጅነት ከዚሁ ቃል አንጻር ተረድተናል፡፡ በክፍል ሁለት ትምህርታችን ደግሞ ማየት ከሚለው ቃል አንጻር የመላእክትን አማላጅነት እንማራለን፡፡

መቆም እንደሚለው ቃል ሁሉ ‹‹ማየት›› የሚለው ቃልም በመጽሐፍ ቅዱስ የራሱ የሆነ አገባባዊ ፍቺ አለው፡፡ በዓይን መለማመጥ፣ ማሳዘን፣ መቆጣት፣ ተስፋ ማድረግ እና ማስፈራራት ይቻላል፡፡ ‹‹የሁሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል፡፡›› እንዲል፡፡ (መዝ 144.15) ስለዚህ ‹‹ማየት›› መመርመር ወይም ንስሐ መግባት፣ መለመን፣ መጸለይ፣ ተስፋ ማድረግ፣ ማማለድ፣ መስማት፣ መቀበል፣ መቆጣት ወዘተ የሚሉ ፍቺዎች አሉት፡፡

ማየት የሚለው ቃል ከ እግዚአብሔር አንጻር

በተለይ ከእግዚአብሔር አንጻር ካየነው ማየት የሚለው ቃል መስማት፣ መቀበል፣ ይቅር ማለት የሚል ትርጉም ይይዛል፡፡ "እግዚአብሔር እገሌን በዓይነ ምሕረት አየው" ማለት አሰበው፣ ጎበኘው፣ ማረው፣ ሰማው ፣ ይቅር አለው ማለት ይሆናል፡፡ እንደ አገባቡ ተቆጣው ማለትም ሊሆን ይችላል፡፡ ለጠቀስናቸው ሐሳቦች ከመጽሐፍ ቅዱስ ‹‹እግዚአብሔርም ወደ አቤልና ወደ መሥዋዕቱ ተመለከተ፡፡››፤ ‹‹እነሆ የእግዚአብሔር ዓይኖች ወደሚፈሩት ናቸው፡፡››፤ ‹‹የእግዚአብሔር ዓይኖች ወደ ጻድቃን ጆሮውም ወደ ጩኸታቸው ነው፡፡›› የሚሉትን ማስረጃዎች መመልከት ብቻ እንኳን ይበቃል፡፡ (ዘፍ 4।4፤ መዝ 32।18፤ 33।15)

ከፍጥረት አንጻር

"ማየት" የሚለውን ቃል ከሰው አንጻር ወይም ከፍጥረት ሁሉ አንጻር ካየነው ደግሞ ሌሎች ፍቺዎች ይኖሩታል፡፡ ‹‹አቤቱ አምላኬ እየኝ ስማኝም፡፡›› ሲል ማረኝ ለማለት ነው፡፡ "ማየት" መመርመር ሲሆን ‹‹ራስህን ለካህን አሳይ›› ይላል፡፡ ይህ ደግሞ ራስህን አስመርምር፣ ንስሐ ግባ ማለት ነው፡፡ (ማቴ8.4፤ መዝ12.3) በእንግሊዝኛውም ይህን የመሰለ ነገር አለ፡፡ ነጮቹ ሕክምና ላድርግ ወይም ልመርመር ለማለት ‹‹ሐኪሜን ልይ›› ይላሉ፡፡

ከላይ በተጠቀሰው መልኩ ‹‹ማየት›› የሚለውን ቃል ትርጉም በትክክል በመረዳት የመላእክትን አማላጅነት በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል፡፡

ለሰው ልጆች በሙሉ ለየራሳቸው ጠባቂ መላእክት አሏቸው፡፡ ይህንንም ያደረገው ፈጣሪ ነው፡፡ ‹‹መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና›› የሚለው የነቢዩ የዳዊት መዝሙር ፈጣሪ ለሰው ልጆች የሚጠብቋቸው መላእክትን እንዳዘጋጀ ያስረዳል፡፡ (መዝ90.11) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌያዊ ትምህርቱ ለበለሱ አትክልተኛ መቅጠሩ በበለስ ለተመሰሉ የሰው ልጆች ለእያንዳንዳቸው ጠባቂና ተንከባካቢ መልአክ ማዘጋጀቱን የሚያስረዳ ነው፡፡ (ሉቃ13.6-9) በትንቢተ ዳንኤል መጽሐፍ ውስጥ መልአኩ ‹‹ቅዱስ ጠባቂ›› የተባለው በዚህ ምክንያት ነው፡፡ (ዳን4.13፤ 4.23) በተጨማሪም ለሰው ልጆች ሁሉ ጠባቂ መልአክ እንዳላቸው በወንጌል ‹‹መላእክቶቻቸው›› በሚል የተቀመጠው ቃል ብቻ ምስክር ነው፡፡ (ማቴ18.10)

መላእክት እንደ ታላላቅ ወንድሞቻችን የምንቆጥራቸው እነርሱም ደግሞ እኛን እንደ ታናናሽ ወንድሞቻቸውና እኅቶቻቸው የሚያዩን ቤተሰቦቻችን ናቸው፡፡ እነርሱ ከእኛ በፊት በዕለተ እሑድ የተፈጠሩ የአምላክ ልጆች ሲሆኑ እኛ ደግሞ በዕለተ ዐርብ የተፈጠርን የእግዚአብሐር ልጆች ነንና፡፡ (ኢዮ1.6፤ 2.1፤ ዮሐ1.12) የአንድ አባት ልጆች ደግሞ ወንድሜ እኅቴ እንደሚባባሉ የታመነ ነው፡፡ ስለዚህ መላእክት እየሳሱ ይጠብቁናልና እኛ የእነርሱ ገንዘብ ነን፡፡ እነርሱም የእኛ ገንዘቦች በመሆናቸው ‹‹መላእክቶቻቸው›› ተብለዋል፡፡ ይህም ከወንጌሉ ትረካ የምናታገነው ነው እንጂ በብልሃት የተፈጠረ ቃል አይደለም፡፡

እነዚህ ጠባቂ መላእክት ስለ ሰው ልጅ የእግዚአብሔርን ፊት እንደሚያዩ ወንጌል ይናገራል፡፡ ‹‹መላእክቶቻቸው ዘወትር በሰማያት ያለውን የአባቴን ፊት ያያሉና›› እንዲል፡፡ (ማቴ18.10) ይህም ዐረፍተ ነገር ያለ ምንም ጥርጥር የመላእክትን አማላጅነት የሚያሳይ ነው፡፡ ማየት መጸለይ ማማለድ የሚል ትርጉም እንዳለው ቀደም ሲል በሚገባ ተቀምጧልና፡፡ ካልሆነ ግን በምን ሊተረጎም ይችላል? የጥቅሱን ሙሉ ሐሳብ ስንወስድ ሰዎችን አትናቁ! የምትንቋቸውን ሰዎች የሚጠብቁ መላእክት ዘወትር የአባቴን ፊት ያያሉ የሚል ነው፡፡ ይህም ለተናቁት ሰዎች ለምነው ያማልዷቸዋል፡፡ የምትንቁትን እናንተን ደግሞ ጸልየው ያስፈርዱባችኋል የሚል ማስጠንቀቀቂያ ቃል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

ለማጠቃለል በቃል የሚጠና ሐሳብና ጥቅስ

ጽንሰ ሐሳብ፡- "ማየት" መጸለይ፣ ማማለድ፣ መስማት፣ መቀበል፣ ይቅርታ ማድረግ ማለት ይሆናል፡፡ እንዲህ ከሆነ መላእክት ስለ እኛ የፈጣሪን ፊት ያያሉ ማለት ያማልዳሉ ማለት ነው፡፡

በቃል የሚጠኑ ጥቅሶች

1ኛ. "ማየት" መስማት፣ መቀበል ሲሆን በፈጣሪ አንጻር

(ዘፍ4.4፤ መዝ32.18፤ 33.15)

2ኛ."ማየት" መጸለይ፣ ማማለድና ይቅርታ መጠየቅ ሲሆን ከፍጡር አንጻር

(ማቴ18.10፤ ማቴ8.4፤ መዝ12.3)

ይቀጥላል

የቅዱሳን መላእክት አማላጅነት - ክፍል አንድ

ቅዱሳን መላእክት አማላጆቻችን ናቸው፡፡ ስለ ቅዱሳን መላእክት አማላጅነት በመጽሐፍ ቅዱስ በስፋት ተጽፏል፡፡ ይህንንም የተለያዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችን በመጥቀስና ትክክለኛ ትርጉማቸውን በምንረዳበት ጊዜ የምናገኘው ነው፡፡
ሐሳቡን በትክክል ለመያዝና ለማጥናት እንዲረዳን የመላእክትን አማላጅነት በስድስት ዋና ዋና መንገዶች ከፍለን ለማየት እንችላለን፡፡
ለዛሬ ከስድስቱ የመጀመሪያውን እነሆ፡-
1ኛ. መቆም የሚለውን ቃል ትክክለኛ ትርጉም በመረዳት፡- መቆም የሚለው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በልዩ ልዩ ቦታዎች አገልግሎት ላይ ውሏል፡፡ እንደየአገባቡም ትርጉሙ የተለያየ ነው፡፡ መቆም የሚለው ቃል ከያዛቸው ትርጓሜዎች አንዱ ማማለድ የሚል ነው፡፡ መቆም ከተኙበት ወይም ከተቀመጡበት መነሣት፣ በእግር ቀጥ ማለት፣ መጽናት፣ በክብር መቀመጥ ወዘተ የሚሉ ሌሎች ትርጓሜያትም አሉት፡፡ ስለዚህ እንደየአገባቡ ታይቶ ይፈታል እንጂ ሁል ጊዜ ቃሉን በአንድ ዓይነት መንገድ ብቻ መመልከት ከስሕተት ላይ ይጥላል፡፡
ለዚህ ሁሉ አገባብ ማስረጃ ብትሻ እነዚህንና ሌሎችንም ጥቅሶች በሚገባ ፈትሽ፡፡ ‹‹የደምዋም ፈሳሽ በዚያን ጊዜ ቆመ›।፣ ‹‹የደመናው ዓምድ ቆመ››፣ ‹‹በሃይማኖት ቁሙ›› (ሉቃ8।44፤ ዘዳ31.15፤ ዘኁ10.12፤ 1ቆሮ16.13) በእነዚህ ጥቅሶች ውስጥ መቆም የሚለው ቃል የተለያየ ሐሳብ ይዞ መገኘቱን ልብ ማለት ያሻል፡፡

አሁን ከዚህ ቦታ ከርእሳችን አንጻር እኛ የምንፈልገው ቆመ የሚለው ቃል ማማለድ የሚል ትርጉም ይዞ መገኘቱን መረዳት ነው፡፡ መቆም ሲባል ማማለድ የሚል ትርጓሜ እንዳለው ለመረዳት ስለ ሊቀ ነቢያት ሙሴ የተጻፈውን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ እስራኤላውያን ጣዖት በማምላክ ፈጣሪቸውን አስቆጡት፡፡ እርሱም ሊያጠፋቸው ጀመረ፡፡ ነገር ግን ሙሴ እነዚህን ሕዝቦች ከምታጠፋ እኔን ከሕይወት መጽሐፍ ደምስኝ በማለት በራሱ ፈርዶ አማለዳቸው፡፡ ፈጣሪም የሙሴን ልመና ሰምቶ መዓቱን በትዕግሥት መለሰ፡፡ ይህ ታሪክ በዘፀአት የኦሪት ክፍል ተመዝግቧል፡፡ (ዘፀ32।32)
ይህንን የሙሴ ምልጃ ቅዱስ ዳዊት በሌላ ጊዜ በድጋሚ ተርኮታል፡፡ ይኸውም በዳዊት መዝሙር የምናገኘው ነው፡፡ ነገር ግን አተራረኩ መቆም ማማለድ መሆኑን በግልጽ በሚያሳይ መንገድ ነው፡፡ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ያዳናቸውን እግዚአብሔርን ረሱ፡፡ እንዳያጠፋቸው ቁጣውን ይመልስ ዘንድ የተመረጠው ሙሴ በመቅሠፍት ጊዜ በፊቱ ባይቆም ኖሮ ያጠፋቸው ዘንድ ተናገረ፡፡›› የተሰመረበትንና ደምቆ የተጻፈውን ኃይለ ቃል ልብ ብለህ ተመልከት፡፡ (መዝ015।23) ባይቆም ኖሮ ሲል ባያማልዳቸው፣ ባይለምንላቸው፣ ባይጸልይላቸው ኖሮ ማለቱ ነው፡፡ ስለዚህ መቆም የሚለው ቃል ማማለድ የሚል ትርጉም እንደሚኖረው እንረዳለን፡፡
ዳግመኛም መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹የእግዚአብሔር ልጆች (መላእክት) በእግዚአብሔር ፊት ለመቆም መጡ፡፡ ሰይጣንም ደግሞ በመካከላቸው መጣ›› ይለናል፡፡ ‹‹ለመቆም›› ሲል ለመለመን፣ ለማማለድ ማለት ነው፡፡ አብሮአቸውም ሰይጣን መምጣቱን ልብ በል፡፡ ሰይጣን የመጣው ለምን ነበር? ጻድቁ ኢዮብን ለመፈተን ፈቃድ ያገኝ ዘንድ ፈጣሪውን ለመለመን አልነበረምን? የመላእክትም አመጣጥ ፈጣሪቸውን ስለሰው ለመለመን እንጂ ለሌላ አልነበረም፡፡ ይህን ሲገልጥ ‹‹ለመቆም መጡ›› ይለናል፡፡ መቆም መለመን፣ ማማለድ ማለት ነውና፡፡ (ኢዮ1।6) መቆም ማለት መጸለይ፣ ማማለድ የሚል ፍቺ እንዳለው ካስጨበጡ በኋላ ይህንን ቃል በመጠቀም የመላእክትን አማላጅነት ማስረዳት ቀላል ይሆናል፡፡

ቃላት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እኛ ከምናውቀው ውጭ አንዳንድ ጊዜ በተቃራኒ አቅጣጫም እንኳን ፍቺ ይዘው ይገኛሉ፡፡ አገባባቸውን እንደመጽሐፍ ቅዱስ ዘይቤና ምሥጢር መማር የሚያስፈልገው ከዚህ የተነሣ ነው፡፡ ለብዙ ሰዎች በመጽሐፍ ቅዱስ የተቀመጡ ቃላትን ትክክለኛ መንፈስ አለመረዳት የመላእክትን አማላጅነት እንዳይረዱ አድርጓቸዋልና፡፡
ለምሳሌ፡- ቅዱስ ገብርኤል ራሱ ‹‹እኔ በእግዚአብሔር ፊት የምቆመው መልአኩ ገብርኤል ነኝ፡፡›› በማለት ተናግሯል፡፡ ይህም በቅዱስ ወንጌል የተጻፈ ኃይለ ቃል ሲሆን አብዛኞቻንን እናውቀዋለን፡፡ ልዩ የሚሆነው ግን የቃሉን ትክክለኛ አገባባዊ ትርጉም ባለማወቃችን ምክንያት መልአኩ ይህን ባለ ጊዜ ‹‹እኔ አማላጅ ነኝ›› እንዳለን አድርገን አለመረዳታችን ነው፡፡ መቆም ማለት ማማለድ የሚል ትርጉም ካለው ‹‹በእግዚአብሔር ፊት የምቆም›› ማለት ደግሞ ‹‹የማማልድ›› ማለት መሆኑ አይጠረጠርም፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ገብርኤል አማላጅነቱን ራሱ ግልጽ በሆነ መንገድ ነግሮናል ማለት ነው፡፡
እስኪ እናንተ ፍረዱ! በዚህ ስፍራ ቅዱስ ገብርኤል አማላጅ ነኝ ማለቱን ካላመንን ‹‹እኔ በእግዚአብሔር ፊት የምቆመው›› ማለቱን ምን ብለን እንረዳዋለን? የእግዚአብሔር ፊቱ ወደ ሁሉም አቅጣጫ ነው እንጂ እንደፍጡር ወደ አንድ ገጽ የተወሰነ አይደለም፡፡ መላእክት ደግሞ በተፍጥሯቸው እንደ ሰው ልጅ የሚታጠፍና የሚዘረጋ እግረ ሥጋ ስለሌላቸው አይቀመጡም፤ አይተኙምም፡፡ ታዲያ አማላጃችሁ ነኝ ማለቱ ካልሆነ በቀር መልአኩ ‹‹እኔ በእግዚአብሔር ፊት የምቆመው›› ሲል ምን ማለቱ ነው? መልአኩ እግዚአብሔርን እንደ ምድራዊ ንጉሥ ራሱን ደግሞ እንደ ንጉሥ ወታደር ቆጥሮ በንጉሡ ፊት ቀጥ ብዬ የምውል ዘበኛ ነኝ ማለቱ ነውን? በፍጹም አይደለም፡፡ በእግዚአብሔር ቤት ደጅ አፍ መቆምና በእግዚአብሔር ፊት መቆም ሁለት የተለያዩ ጉዳዮች ናቸው፡፡ ምሥጢራቸውም እንዲሁ የተለያየ ነው፡፡ (ራእ21।12፤ ዘፍ3.24) ይልቅ ሊሆን የሚችለው እኔ በፊቱ ባለሟልነት ያለኝ ሁሉ ጊዜ ስለ እናንተ የማማልድ ነኝ የሚል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
መልአኩ በእግዚአብሔር ፊት የሚቆመው ለምንድን ነው? ለማመስገን ነው እንዳንል ይህንን ሐሳብ ለካህኑ ለዘካርያስ መንገር ለምን አስፈለገው? የሚል ጥያቄ ያስነሣል፡፡ ትርጉሙ እንዲህ ቢሆን ወደ ካህኑ ወደ ዘካርያስ ከመጣበት ጉዳይ ጋር ንግግሩ ምንም ግንኙነት አይኖረውምና ይህን መናገር አያስፈልገውም፡፡ ከዚህ ይልቅ እኔ ሰዎችን ሁሉ ለማማለድ በእግዚአብሔር የምቆም ባለሟልነት ያለኝ መልአክ በመሆኔ የለመንከው ልመና መድረሱን የምሥራች ልነግርህ ብመጣ ቃሌን እንዴት ትጠራጠራለህ? ለማለት ‹‹እኔ በእግዚአብሔር ፊት የምቆመው መልአኩ ገብርኤል ነኝ›› በማለት መልአኩ ይህን ተናገረ ብንል ከሁሉ በላይ የሚያስኬድና ለአእምሮ የሚመች ትክክለኛ ትርጓሜ ነው፡፡
በተመሳሳይ መልኩ ስለ ቅዱስ ሚካኤልም በትንቢተ ዳንኤል ላይ እንዲህ ተጽፏል፡፡ ‹‹በዚያ ወራት ስለ ሕዝብ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል›› ይላል፡፡ (ዳን12.1) በዚህ ጥቅስ ቅዱስ ሚካኤል ‹‹ስለ ሕዝብ ልጆች የሚቆመው›› ተብሏል፡፡ እረ ለመሆኑ ቅዱስ ሚካኤል ስለ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት ‹‹የሚቆመው›› ለምንድር ነው? ለማማለድ አይደለምን? ይህን ካልተቀበልን ቃሉን ምን ብለን እንተረጉመዋለን? ለማመስገን ይቆማል እንዳንል ቃሉ የሚለው ‹‹ስለ ሕዝብ ልጆች የሚቆመው›› ነው፡፡ ስለ እኛ ጥብቅና ይቆማል እንዳንል ወደ ባሰ ስሕተት ይወስደናል፡፡ ሚካኤል በእግዚአብሔር ፊት ጥብቅና አይቆምምና፡፡ እግዚአብሔርም በጠበቃ የሚሟገቱት አምላክ አይደለምና፡፡ ጥብቅና ይቆማል ከማለት ይልቅ ትክክለኛውና የሚስማማው ወደ ፈጣሪ ሊለምንልን ወይም እኛን ለማማለድ ይቆማል የሚለው ትርጓሜ ነው፡፡ አስቀድሞ እንደተመለከትነው ‹‹መቆም›› የሚለው ቃል ማማለድ የሚል ትርጉም አለውና፡፡
ይህ ለምሳሌ ያህል ተጠቀሰ እንጂ በፈጣሪ ፊት እልፍ አእላፋት መላእክት ለምልጃ ይቆማሉ፡፡ ቅዱስ ዳንኤል ‹‹ሺህ ጊዜ ሺህ ያገለግሉት ነበር፡፡ እልፍ አእላፋትም በፊቱ ቆመው ነበር፡፡›› በማለት የገለጸው ይህንን እውነት ነው፡፡ (ዳን7.9-11)
ከዚህ በላይ ከብሉይ ስለ ቅዱስ ሚካኤል ከሐዲስ ደግሞ ስለ ቅዱስ ገብርኤል የተጻፉት ለማስረጃነት ተጠቅሰዋል፡፡ የተማሩትንና ያነበቡትን በልብ ለመክተብ መላልሶ ማንበብና ማጥናት እንደሚያስፈልግ እሙን ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ብትሻ የቅዱስ ገብርኤል ዝክረ በዓል ወር በገባ በአሥራ ዘጠኝ እንደሚውል ታውቃለህ፡፡ ስለ እርሱም የተጠቀሰው በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 1.19 መሆኑን ልብ በልና ጥቅሱ ከወርኃዊ በዓሉ ጋር ያለውን ዝምድና መርምር፡፡ ማለትም ቁጥር 19 ላይ መጻፉን አስተውል፡፡ ስለ ቅዱስ ሚካኤልም እንዲሁ አድርግ፡፡ ጥቅሱ በትንቢተ ዳንኤል ምዕራፍ 12 ላይ ይገኛል፡፡ የቅዱስ ሚካኤል ወርአዊ ክብረ በዓሉም በ12ኛው ቀን ላይ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ስለዚህ ይህንንና ይህን የመሰለ የራስህን የማጥኛ ዘዴ በመጠቀም ጥቅሶቹን በቃልህ ለማጥናት ሞክር፡፡
ለማጠቃለል በቃል የሚጠና ሐሳብና ጥቅስ

ጽንሰ ሐሳብ፡- መቆም ማማለድ ማለት ይሆናል፡፡ የዚህ ማስረጃው (መዝ105.23፤ ኢዮ1.6) ነው፡፡ እንዲህ ከሆነ መላእክት ስለ እኛ በፈጣሪ ፊት ይቆማሉ ማለት ያማልዳሉ ማለት ነው፡፡
በቃል የሚጠኑ ጥቅሶች
1ኛ।ሉቃ1:19
2ኛ।ዳን12:1
3ኛ।ዳን7:9-11

እነዚህን ማጥናት አያቅትምና አጥንቶ ለልጆች በማስጠናት የወላጅነት ግዴታችንን በዚህ መንገድ እንወጣ!
ይቆየን!
ከዲያቆን ኅብረት የሺጥላ

20111229

ኢየሱስ ክርስቶስ ማን ነው ? ክፍል አምስት በ መምህር ታሪኩ አበራ

ኢየሱስ ክርስቶስ ማነው? ክፍል አራት በመምህር ታሪኩ አበራ

ኢየሱስ ክርስቶስ ማነው? ክፍል ሦስት በ መምህር ታሪኩ አበራ

ኢየሱስ ክርስቶስ ማን ነው? ክፍልሁለት በመምህር ታሪኩ አበራ

ኢየሱስ ክርስቶስ ማነው ? ክፍልአንድ በመምህር ታሪኩ አበራ

ማርያም ሆይ በቀሲስ ዘበነ ለማ

ክብር ለሚገባ ክብርን ስጡ በ መምህር ታሪኩ አበራ

የ አሁኑ ይባስ !! በመምህር ምህረትአብ አሰፋ

ፕሮቴስታንታዊ ጅሃድ በ መምህር ምህረትአብ አሰፋ

ከልደት በዓል በፊት ያሉት ሦስቱ የጾመ ነቢያት ሳምንታት

ከልደት በዓል በፊት ያሉት ሦስቱ የጾመ ነቢያት ሳምንታት
እነዚህ ከልደተ በዓል በፊት ያሉት ሦስቱ የጾመ ነቢያት ሳምንታት ስብከት፣ ብርሃን እና ኖላዊ ተብለው ይጠራሉ፡፡
እነዚህ ሳምንታት ነቢያት አምላክ ይህንን ዓለም እንዲያድን ያላቸውን ናፍቆት የገለጡባቸው እና ይህንን አስመልክተው ያስተማሩባቸው ሦስት የተለያዩ መንገዶች እና ጌታችንም ለእነዚህ መልስ የሰጠባቸው ሁኔታዎች ይታሰቡባቸዋል፡፡
1. ስብከት ( ከታኀሳስ ፯ እስከ ታኅሳስ ፲፫ )
ስብከት ማለት ማስተማር ማለት ነው፡፡ ይህ ሳምንት ከሙሴ ጀምሮ የነበሩ ነቢያት በሙሉ አዳኝ /መሲህ/ እንደሚመጣ ማስተማራቸው ጌታችንም እነርሱ ይመጣል ብለው ያስተማሩለት እኔ ነኝ ብሎ ራሱን መግለጡ የሚታሰብበት ነው፡፡
ሙሴ ለጊዜው የጌታችን ምሳሌ ለሆነው ለኢያሱ ፍጻሜው ግን ለጌታችን በሆነው ትንቢቱ «አምላክህ እግዚአብሔር ከወንድሞችህ እንደ እኔ ያለ ነቢይ ያስነሳልሃል፤ እርሱንም ስሙት፡፡
» ብሎ ለሕዝበ እስራኤል ነግሯቸው ነበር፡፡ /ዘዳ. 18.15/ እግዚአብሔር ወልድም በሥጋ ማርያም በተገለጠ ጊዜ ራሱን ያስተዋወቀው ያ ነቢያት የተናገሩለት አዳኝ /መሲህ/ እንደሆነ ነው፡፡ «ሙሴ እና ነቢያት ሁሉ ስለ እኔ ይናገራሉ፡፡» ይላቸው ነበር፡፡ ትንቢቱን ያውቁ የነበሩ በእግዚአብሔር መንገድ የሚሄዱ እስራኤላውያንም «መሲሁን አገኘነው»፣ «ሙሴ በህግ መጻሕፍት፣ ነበያትም ስለ እርሱ የጻፈለትን የናዝሬቱን ኢየሱስን አገኘነው» እያሉ ተከትለውታል፡፡ /ዮሐ. 1.41፣ ዮሐ. 1.45/ ሐዋርያትና ሌሎቹ ደቀመዛሙርቱም ከጌታችን ሞትና ትንሳኤ በተለይ የተነገሩትን ትንቢቶች ሁሉ ያውቁ ለነበሩት እስራኤላውያን ያስተማሩት እነዚህን የነቢያት ትምህርቶች እና ትንቢቶች እየጠቀሱ ነበር፤ ቅዱስ ጴጥሮስን በቤተ መቅደስ እንዲህ ብሎ አስተምሯል፤ «አሁንም ወንድሞቼ ሆይ አለቆቻችሁ እንዳደረጉ ይህን ባለማወቅ እንዳደረጋችሁት አውቃለሁ፡፡ እግዚአብሔር ግን ክርስቶስ መከራን እንዲቀበል በነቢያት ሁሉ አፍ እንደተናገረ እንዲሁ ፈፀመ» /ሐዋ. 3.17-18/፡፡ በሁለተኛው መልእክቱ ደግሞ እንዲህ ሲል ጽፏል፡- «ወንድሞች ሆይ የቀደሙ ቅዱሳን ነቢያት የተናገሩትን ቃልና ለእኛ ለሐዋርያትም ያዘዘውን የመድኃኒታችንና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ትእዛዝ ታስቡ ዘንድ... ዕወቁ» /2ኛ ጴጥ. 3.1-3/ ቅዱስ ጳውሎስም በዕብራውያን መልእክቱ መግቢያ ላይ እንዲህ ብሏል፤ «ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዐይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናገረ፤ በኋላ ዘመን ግን ሁሉን ወራሽ ባደረገው፣ ሁሉን በፈጠረበት በልጁ ነገረን፡፡» /ዕብ. 1.1-2/
2. ብርሃን (ከታኀሳስ ፲፬ እስከ ታኅሳስ ፳)
ነቢያት የአምላክን ማዳን ከጠበቁባቸው እና ከገለጡባቸው መንገዶች አንዱ ብርሃን ነው፡፡ ዘመነ ብሉይ መከራ ሥጋ፣ መከራ ነፍስ የፀናበት፣ ሁሉ ነገር አስጨናቂ የሆነበት፣ ሰው ብርሃን ከሆነው አምላክ ጋር የተራራቀበት ስለነበር ያሉበትን ዘመን «ጨለማ» ብለው በመግለጥ ይህንን ጨለማ የሚያስወግድና ወደ ትክክለኛው መንገድ የሚመራ ብርሃን እንዲመጣ እንዲህ እያሉ ይፀልዩ ነበር፡፡ «ብርሃንህንና ጽድቅህን ላክ፣ እነርሱም ይምሩኝ፣ አቤቱ ወደ መቅደስህ ተራራና ወደ ማደራያህ ይውሰዱኝ» /መዝ. 42.3/ ጌታችንም ወደዚህ ዓለም በመጣ ጊዜ ለዚህ መልስ ሰጥቷል፤ «እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ» /ዮሐ. 8.12/ ደቀመዛሙርቱም ስለ ብርሃንነቱ በመመስከር ተባብረዋል፤ - ቅዱስ ዮሐንስ ስለጌታችን ሰው መሆን /ሥጋዌ/ በተናገረበት በወንጌሉ የመጀመሪያ ክፍል ጌታችንን ብርሃን ብሎታል፤ «ሕይወት በእርሱ ነበረ፣ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረ፤ ብርሃንም በጨለማ ያበራል፤ ጨለማም አላሰነፈውም» /ዮሐ. 1.4-5/ ቅዱስ ጳውሎስም ጌታችን በሚያንፀባርቅ ብርሃን አምሳል እንደተገለጠበት ተናግሯል፡፡ «እኩል ቀን በሆነ ጊዜ በመንገድ በሄደ ከፀሐይ ይልቅ የሚበራ መብረቅ በእኔና ከእኔ ጋር ይሄዱ በነበሩት ላይ ከሰማይ ሲያንፀባርቅ አየሁ፤ ... አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ አለኝ፡፡» /ሐዋ. 26.13/
3. ኖላዊ (ከታኀሳስ ፳፩ እስከ ታኅሳስ ፳፯ )
ኖላዊ ማለት እረኛ ማለት ነው፡፡ ነቢያቱ ራሳቸውን እና ሕዝበ እስራኤልን ብሎም ዓለምን እረኛቸው እንደተዋቸው እና እንደተቅበዘበዙ በጎች በመቁጠር እንዲሰበስባቸውና እንዲያሰማራቸው እንዲህ እያሉ እራሳቸውን ይማፀኑ ነበር» «ዮሴፍን እንደ መንጋ የምትመራ የእስራኤል ጠባቂ /እረኛ/ ሆይ፣ አድምጥ በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ ተገለጥ፡፡» /መዝ. 79.1/ ጌታችንም ለዚህ ጥያቄ እንዲህ ሲል መልስ ሰጥቷል፤ «ቸር ጠባቂ /እረኛ/ እኔ ነኝ፡፡ ቸር ጠባቂ ስለ በጎቹ ነፍሱን ይሰጣል፡፡» /ዮሐ10.11/

20111227

የመላዕክት አለቃ


የመላዕክት አለቃ ገብርኤል ቅዱስ
የምስራች ነጋሪ መጋቢሐዲስ
በዙሪያቸው ከሞት የሚፈሩትን
ይታደጋቸዋል ከሥቃይ እቶን
እሳቱን አጥፍቶ በበትረመስቀሉ
ሲዘምሩ ዋሉ ይትባረክ እያሉ
መከራው ጸንቶብን ጨንቆን ስንጠራው
ሳይዘገይ ይደርሳል በግሩም ግርማው
ግና በሐጥያት ብናስመርረው
ይቀስፈናል የአምላክ ሲም በእርሱ ላይ ነው

ቅዱስ ገብርኤል


ታህሳስ 19 ቀን በዚህ ቀን ሰለስቱ ደቂቅ "የምናመልከው አምላካችን ከሚነደው ከእሳቱ እቶኑ ሊያድነን ይችላል" ያሉበት ዕለትና ቅዱስ ገብርኤል ከእሣት ያዳቸው ዕለት መታሰቢያ በዓል ነው። ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን አባቶቻችን እንዳስተማሩን ነገሩ እንዲህ ነው። ዘመኑ ጣኦት የሚመለክበት ንጉስ ናቡከደነፆር የእግዚአብሔር ሰዎች የቅዱስ ገብርኤል ወዳጆች የነበሩት ወጣቶች ሥም አናንያ (ሲድራቅ) ፤ አዛርያ (ሚሣቅ) ፤ ሚሣኤል (አብድናጎ) ነበሩ። ት/ዳንኤል 3፡1-30 ታሪኩ እንደሚግረን ንጉስ የጣኦት ምስል አሰራ በገሊላ አውራጃ ያለውን ሕዝብ ጠርቶ ለጣኦቴ ያልሰገደ ወደ እሣት ውስጥ ይጣላል ብሎ አወጀ። በዚህ መካከል ሰልስቱ ደቂቅ ነበሩ። የንጉስ ትህዛዝ ነውና ሕዝቡ ሁሉ ለጣኦቱ ሲንበረከክ እነርሱ ግን ቆመው ያዩ ነበር። የእግዚአብሔር የሆነ ሰው ምንም ነገር አያስፈራውምና ናቡከደነፆር እርሱ ላስቆመው ጣኦት አለመስገዳቸውን ሲሰማ ተናደደ ፤ ተበሳጨም እሳቱን 7 እጥፍ እንዲነድ አስደረገ ሦስቱንም አስሮ እሣቱን እያሳየ "ከመቃጠል ወይስ ለእኔ ጣኦት መስገድ የቱ ይሻል?" ባላቸው ጊዜ የምናመልከው አምላካችን ከሚነደው ከእሳቱ እቶን ሊያድነን ይችላል ባያድነንም እንኳን አንተ ለመታመልከው ጣኦት አንሰግድም አሉት ። በዚህ ጊዜ ጉልበት ያላቸው ሠዎች ተፈልገው ሦስቱን ወጣቶች አስረው ወደ እሣት ቶን ውስጥ ጣሏቸው አስረው የጣሉቸው ወታደሮች የእሣቱ ወላፈን አቃጠላቸው ሠልስቱ ደቂቅን ግን መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ እሳቱን አበረደላቸው አጠፋላቸው ። በዚህም ጊዜ ንጉስ ናቡከደነፆር እንዲህ በማለት መሰከረ "እኛ አስረን የጣልናቸው ሦስት ነበሩ አሁን ግን አራተኛው ሰው በእሳቱ ሲመላለስ ይታየኛል እንዲያውም የአማልክትን ልጆች ይመስላል " አለ። የእግዚአብሔር የማዳኑ ስራ ሲገለጥ ቅዱስ ገብርኤል ሲታይ አዋጁ ሁሉ ተሻረ ጉልበት ሁሉ ለጣኦት ተብሎ የነበረው "ጉልበት ሁሉ ለሰልስቱ ደቂቅ አምላክ ይስገድ ይንበርከክ" ተባለ ይህን ሁሉ ታህሳስ 19 ቀን ሆነ በዚህም ምክንያት በታላቅ ደስታ እናከብረዋለን ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የመላእክት የቅዱስ ገብርኤል ጥበቃው ረድየት በረከቱ አይለየን

20111225

ቅድስት እንባመሪና


የቅድስት እንባመሪና እናት ማርያም ትባላለች ገናም ህጻን እያለች ነበር በሞት የተለየቻት ከዛም አባቷ ለአቅመ ሄዋን እስክትደርስ ድረስ በጎ ትምህርቶችን ሲያስተምራት አሳደጋት በኋላም ለአቅመ ሄዋን ስትደርስ አጋቧት::እርሱ ወደ መነኮሳት መኖሪያ ሄዶ ሊኖር እንደወደደ ሲነግራት እጂግ አልቅሳ "አባቴ ያንተን ነፍስ አድነህ የኔን ነፍስ ማጥፋት እንዴት ይሆንልሃል ?" አለችውና አባቷም እኔ የምሄደው ወደ ወንድ መነኮሳት ነው አንቺን ደግሞ ሴት ነሽ አያስገቡሽም ሲላት እንደወንድ ሱሪ አድርጌ ጸጉሬን ተቆርጬ ወንድ መስዬ ካንተ ጋር ሄዳለው አለችውና::ያላቸውን ንብረት ሁሉ ሽጠው እና ለደሃ መጽውተው ተያይዘው ገዳም ይገባሉ:: በዚያም ገዳም እጅግ እየተጋደሉ ኖሩ:: በኋላም አባቷ በጸና ስለታመመ አበ ምኔቱን አስጠርቶ ልጄን አደራ በምንም መልኩ ከገዳም እንዳይወጣብኝ ይልና አበ ምኔቱን አደራ ይለውና ያርፋል::ቅድስት እንባመሪናም ተጋድሎዋን ከቀድሞ እጅግ አብዝታ ትተጋ ጀመር:: ከረጅም ግዜ በኋላም የገዳሙ መነኮሳት ይሄ መነኩሴ ከኛ ጋር ለምንድን ነው ከገዳም ውጪ ለተልኮ የማይወጣው እያሉ አበ ምኔቱን አስጨነቁት በኋላም አበ ምኔቱ ከመነኮሳቱ ጋር አብሮ ይሰዳት ጀመር የሚሄዱትም የገዳሙን ምግብ በየግዜው ከሚሰበስብላቸው አንድ ሰውዬ ቤት ነበር: እንዳስለመዱት በየግዜው ሲሄዱ አንድ ቀን ምግቡን የሚሰጣቸው ሰውዬ አንዲት ልጅ አለችውና ጎረቤት የሆነ አንድ ጎረምሳ ተደብቆ ይገባና የሰውዬውን ልጅ ድንግልናዋን ያፈርሳል በኋላም አባትሽ ማነው እንዲ ያደረገሽ ብሎ ከጠየቀሽ እንባመሪና ነው በይ ይላትና ይሄዳል:: ልጅቷ ታረግዛለች በኋላም አባትየው ከማን እንዳረገዘች ሲጠይቃት ከመነኩሴው ከእንባመሪና ነው አለችው::

ከዛም ያ ሰውዬ ወደ ገዳሙ ይመጣና ባአደባባይ መነኮሳቱን ይረግማቸው ጀመር ከዛ አበ ምኔቱ መጣና ምን ሆነህ ነው ቢለው ልጄን ያንተ መነኩሴ ደፍረብኝ ሲለው ታድያ ባንድ ሰው ጥፋት እነዚን ሁሉ ቅዱሳን ለምን በአደባባይ ትረግማለህ አለውና እንባመሪናን አስጠራት:መጣችና አቤት አባቴ ስትል ሁሉም ይሰድቧት ጀመር ለምን እንደሚሰድቧት ባታቅም ሰይጣን የሰራባት ነገር እንዳለ ገባት እና ዝም አለች:: በኋላም ነገሩን ነገሯት እና አበ ምኔቱ "እንባመሪና ይህ የመነኩሴ አይደለም የአለማውያን ባህሪ አይደለም የሴጣን እንጂ ይህን ለምን አደረክ?"ብሎ ቢጠይቃት እርሷም አባቴ ይቅር በለኝ ወጣትነት አታሎኝ ነው አባቴ ይቅር በለኝ ብላ አበ ምኔቱ እግር ስር ወደቀች::

በኋላም አበ ምኔቱ ከገዳሙ አባረራት እና ከገዳሙ ውጪ ሆና ትጋደል ጀመር ያቺም ልጅ ስትወልድ አባቷ ልጁን አምጥቶ
ለእንባመሪና ሰጣት እንባመሪናም ለልጁ የሚሆን ወተት እና ምግብ በአካባቢው ያሉትን እረኞች እየለመነች አሳደገችው::
ከ3 አመት በኋላም መነኮሳቱ አበ ምኔቱን ለመኑት ባይሆን ከባድ ቀኖና ይሰጠውና ወደ ገዳም ይግባ አሉት:አበ ምኔቱም ልመናቸውን ተቀብሎ ከባድ ቀኖና ሰጣት እና ስትጨርስ ወደ ገዳሙ ተቀላቀለች ከዛም ገዳሙ ውስጥ ያሉትን ከባድ ስራዎች ያሰራት ጀመር ከዛም በኋላ ገዳም ውስጥ ጭንቅ የሆኑ ስራዎችን ያሰሯት ጀመር የመነኮሳቱን ቤት ጠርጋ ተሸክማ ወስዳ ከገዳም ውጪ አውጥታ ትጥላለች: ያም የተወለደ ልጅ አድጎ እዛው መነኮሰ 40 አመትም ከተፈጸመ በኋላ ቅድስት
እንባመሪና 3ቀን ታማ አረፈች:: ከዛም የገዳሙ መነኮሳት ተሰብስበው ደውል ደውለው ተሰበሰቡ ሊገንዟትም ፈልገው ልብሷን ሲያዎልቁት ሴት ሆና ሲያገኟት እጅግ አዝነው አበ ምኔቱን አስጠሩት:አበ ምኔቱም የተፈጠረውን አይቶ እጅግ አዝኖ አለቀሰ ያለበደሏ የሰጣትን ቅኖና እና የተናገራትን ተግሳጽ እያሰበ አምርሮ ያለቅስ ጀመር:: ከዛም ያን የልጅቷን አባት አስጠርቶ የሆነውን ሁሉ ነገረው ከዛም በድንዋን ተሸክመው አቤቱ ይቅር በለኝ እያሉ ዋሉ ማምሻውን ላይ የቅድስት እንባመሪና አስክሬን "እግዚአብሔር ይቅር ይበላቹ" ሲላቸው አውርደዋት በታላቅ ክብር ከስጋዋም ተባርከው ቀበሯት ከመቃብሯም እጅግ ብዙ የሆነ ድንቆች ተአምራት ተደረጉ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚች ጻድቅ ጸሎት ይማረን: ይቅርም ይበለን የቅድስት እንባመሪና በረከት አይለየን አሜን !!!

ቅድስት ማርያም ግብጻዊት



የኢየሩሳሌም ሊቀፓፓስ ሳፍሮኒዮስ እንደጻፈው:- ቅድስት ማርያም ግብጻዊት የተወለደችው በግብጽ ነዉ::ከዚያም የዝሙት ፍቅር አድርባት:ለ17 አመት ያህል ሰዎችን በሚያቃጥል የኃጥያት እሳት ታስፈጃቸው ነበር ዝሙት እየሰራች:ብዙዎችንም ታስት ነበር:: ዝሙት ከመውደዷ የተነሳ ገንዝብ እንኳን ልስጥሽ ሲሉ አትቀበልም ነበር:: በእግዚአብሔርም አታምንም ነበር በዛው ፋንታ እንደፈለገች ትሆን ነበር:: በልቧ ከዚህ ስራዬ ማንም አይከለክለኝም ትል ነበር:: አንድ ቀን ሊቢያውያን እና ግብጻውያን ወደ ባህር እየተቻኮሉ ሲሄዱ አይታ ወዴት እንደሚሄዱ ብጠይቃቸው የከበረ የጌታችንን መስቀል በዓል ለማክበር ወደ እየሩሳሌም እንደሚሄዱ ሲነግሯት እና የሚሄደው ሰው ብዙ መሆኑን ስታይ: ብዙ ዘመዶችን አገኛለው ብላ ከእነርሱ ጋር ለመሄድ ተነሳች:ለጉዞዋ ወይም ለምግብ የሚሆን አንድም ገንዘብ አልያዘችም ነበር:: በኃላም በሰውነቷ ማማር ብዙዎችን በዝሙት ምክንያት አጠመደች ወደ ተቀደሰ ቦታ የሚሄዱቱን ሰዎች በማሳት ዋና የሰይጣን መረብ ሆና ነበር:: በዚህም ስራዋ እየተኩራራች ለሰው ሁሉ ትናገር ነበር:የሐጥያተኛን ሞት የማይወድ እግዚአብሔር መመለሷን እየጠበቀ ይታገሳት ነበር:: በመጨረሻም እየሩሳሌም ደርሰው ከበዓሉ በፊት እንደለመደችው እንደውም በከፋ መልኩ ዝሙትን አብዝታ ትሰራ እና ሰውንም ታስት ነበር:: የበዓሉ ዕለት ጠዋት ብዙ ተሳላሚዎች ጌታችን መቃብር ላይ ወደ ተሰራችው ቤተ-ክርስቲያን ሊሳለሙ ሲሄዱ አየችና እዛ ሄደው ምን እንደሚያደርጉ ለማወቅ ፍላጎት አደረባት እናም ህዝቡ በሚገቡበት በር እየተጋፋች ለመግባት ትሞክር ጀመር በኃላም በሩ ጋር ስትደርስ የሆነ ሐይል ሲገፋት ይታወቃት ጀመር ሌሎቹን ሰዎች ስታይ በቀላሉ ሲገቡ ታያለች መጀመሪያ ላይ ምንድን ነው እያለች ትስቅ ነበር ደጋግማ ስትሞክር አልቻለችም በኃላም ዝም ብላ በሩ ላይ ቆመች እንደገናም ደጋግማ ሞከረች ልትገባ ግን አልቻለችም !! ሲደክማት ብላ ከበሩ አጠገብ ቆመች በህሊናዋም በብዙ መከራ ምን እንደሆነ ታስብ ጀመር:: ቅዱስ መስቀሉን ለማየት እርሷ ያልቻለችበትን ምክንያት ታስብ ጀመር:የድህነት ቃል የልቦናዋን አይኖች ነካቸው እንዳልገባ የከለከለኝ የራሴ ሃጥያት ስትል አሰበች (ተረዳች):: በኃላም በማልቀስ እና ደረቷን እየደቃች ከውስጣዊ ልቧማዘን ጀመረች:: "ለምን አልገባም? እንዳልገባ የከለከለኝ የኃጢአቴ ብዛት ነውን?" እያለች ደጋግማ እራሷን ትጠይቅ ጀመር:: ያን ግዜ የእመቤታችንን የቅድስት ድንግል ማሪያምን ስዕል ከበሩ ላይ አየችና ሄዳ ስዕሉ ፊት ቆማ የስዕሉን ግርማና ውበት ባየች ግዜ ያለፈ የእራሷ ሃጥያት ወለል ብሎ ታያት እና አፈረች::ከዚህም በኃላ በብዙ ለቅሶ ከ ቅድስት ድንግል ማሪያም ስዕል ስር ወድቃ "ከእንግዲህ በኃላ ለጌታየ አገልጋይ ለአንቺም ባርያ እሆን ዘንድ እድል አገኝ ይሆን ?" እያለች ታለቅስ እና ትለምን ጀመር:ጌታችንንም ካለችበት ስቃይና መከራ እንዲያድናት እና በመንገዱ እንዲመራት ለመነችው:"ቅዱስ መስቀሉን ካየው በኃላ አለም እና ደስታዋን እንደምክድ ቃል ገባለው" ብላ ቃል ገባች:: ከጸለየችም በኃላ የመተማመን ስሜት ተሰማትና ወደ መስቀሉ ቦታ ወደሚያስገባው ቦታ ሄደች ከዚያም ያለችግር ገባች በኃላም መስቀሉ ጋር ደርሳ በመንቀጥቅጥ እና በብዙ እምባ ሳመች የእግዚአብሔርን ሚስጥር እና ንስሃን እንዴት እንደሚቀበል አየች:: ከዚያም ወጣ ቃል ወደ ገባችበት ወደ እመቤታችን ስዕል ጋር ሄዳ "የኃጥአንን ንሰሐ ባንቺ አማላጅነት የሚቀበል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን!! አሁን የገባውትን ቃል እፈጽም ዘንድ ግዜው ነው እጄን ይዘሽ ወደ ንስሃ ምሪኝ" አለች:: ያን ግዜ የእመቤታችን ስዕል አፍ አውጥታ "ዮርዳኖስን ብትሻገሪ እረፍት ታገኛለሽ" አለቻት:ከዛም እመቤቴ ሆይ አትተዪኝ ብላ አለቀሰች እና ከዚያ ተነስታ ወደ በረሃው ጉዞ ጀመረች ከመንገዶኞቹም አንዱ እህቴ ሆይ እንኪ ብሎ 3 ሳንቲም ሰጣት እና በእነርሱ ለመንገዷ የሚሆን ዳቦ ገዝታ እያለቀሰች ከከተማው ወጣች:መንገድ ላይም መሸባትና የዮሃነስ መጥምቅ ቤት-ክርስቲያን አግኝታ እዛው ስታለቅስ አደረች:: ጠዋትም አስቀድሳ እመቤታችንንም አንቺ ተከተይኝ እያለች ጉዞዋን ጀመረች ጀልባም ፈልጋ ዮርዳኖስን ተሻገረች ከዚያም ወደ አንድ በረሃ ደረሰች:: በዚያም እህልም ሰውም ሳታገኝ ለ47 አመታት እየተጋደለች ወደሱ የሚመለሱትን ከሚቀበል ፈጣሪ ጋር ኖረች::


ከ47 አመትም ከዚህ በኋላ ዞሲማስ የተባለ መነኮስ እመቤታችን አነሳስታ ልካው ቢሄድ ከሩቅ አያት :: ዕርቃኗን ነበረችና ተነስታ ሮጠች :: (እጅግ ከመክሳቷ የተነሳም ሰው መሆኗ አያስታውቅምም ነበር ):: ዞሲማስም ያየሁት ምንድነው ? በረከት ቀረብኝ ብሎ ተከትሏት ሮጠ :: ጥቂት ተሯሩጠውም ወደ ጉድጓድም ገባች :: መለስ ብላም "ከእኔ ጋር ልትነጋገር ከወደድክ እርቃኔን ነኝና ጨርቅ ጣልልኝ " አለችው :: እርሱም መደረቢያውን ጣለላት :: ያንን ለብሳ ወጥታ እጅ ተነሳሱ :: ስላሳለፈችው እና ስለነበራት ህይወት አጫወተችው:ከዛም ለመጀመሪያው 17 አመታት የነበረባትን ፈተና እንዲ አለችው ""አባት ዞሲማስ ሆይ 17 አመት በዚ በረሃ ከአራዊት ከክፉ ምኞት እና ከክፉ ህሊና ጋር ስታገል ኖርኩ:ያለፈ ህይወቴንና ያሳለፍኩትን ደስታ እያሰብኩ እፈተን ነበር:ከረሃብ እና ከውሃ ጥም እንዲሁም ከጸሃይ ሃሩር የተነሳ በጣም ተሰቃይቻለው: ብዙ ግዜ እታመምና ለሞት እደርስም ነበር: ጌታዬም እንዲረዳኝ እለምነው ነበር ህሊናየን መጀመሪያ ወደ ተቀበለችኝ እመቤቴም ስዕል እሄድና እማጸናት ነበር ከዛም በኃላ በ4ቱ ማእዘን የሚያበራ ብርሃን አይ ነበር""እያለችና ሌላም ሌላም ትነግረው ነበር:ከዛም ቅድስት ማሪያም ግብጻዊት በብዙ ተጋድሎ ሰይጣንን ድል ነስታ ቅዱስ ዞሲማሲን በሚቀጥለው አመት ወደዚ በረሃ ስትመጣ የጌታችንን ቅዱስ ስጋውንና ክቡር ደሙን በዕለተ "ፀሎተ-ሃሙስ" ይዘህልኝ በዮርዳኖስ ባህር ዳር እንገናኝ አለችው ና ተመልሳ ወደ በረሃው ገባች በአመቱን ቅዱስ ዞሲማስ ይዞላት መቶ የዮርዳኖስ ባህርን እየተራመደች ስትመጣ ግዜ አይቶ እግዚአብሄርን እያመሰገነ ቅዱስ ስጋውንና ክቡር ደሙን አቀበላት ከዚያም እንደገና ቅዱስ ዞሲማስን አሰናበተችውና በሚቀጥለው አመት እንዲመጣ ነገረችው በኃላም በዓመቱ ሲመጣ አጣት እና እጂግ አለቀሰ ከዚያም ፈልጎ እሬሳዋን አገኘውና ስሟን ባለማወቁ ሲጸጸት ጊዜ አንድ ብጣቂ ወረቀት አገኘና አነበባት "" አባት ዞሲማስ ሆይ በጸሎተ ሃሙስ ማታ ከቅዱስ ሚስጥር ከተቀበልኩ በኃላ ወደ አምላኬ ሄጃለው የደካማይቱን የማርያምን ስጋ በዚህ ቦታ ቅበረው ዓፈር ወደ ዓፈር ይመለስ ዘንድግድ ነው እና ስለ እኔም ጸልይልኝ ስሟን በማወቁ ደስ እያለው እዛው ቀበራት እና ወደ ቤቱ ተመለሰ:: ቅድስት ማርያም ግብጻዊት ያረፈችው በሚያዚያ 6,522ዓ.ም. ነው:: በረከቷ ረድኤቷ በሁላችን ላይ ይደር !! አሜን !!!!

20111222

ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል


የሰው ልጅ በገነት እንደ ቅዱሳን መላእክት በቅድስና አምላኩን በማመስገን በደስታ ይኖር ነበር ፡፡ ነገር ግን “ክፉና ደጉን ከምታሳውቀው ዕፀ በለስ እንዳትበላ” ተብሎ የተሰጠውን ትእዛዝ በመተላለፉ ምክንያት ከአምላኩ ተለየ(ዘፍ.3፡6) ፡፡እግዚአብሔር በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረው ሰው ክብሩን አጣ፣ ጸጋው ተገፈፈ ፣ ፈጣሪውንም አሳዘነ ፡፡ ቅዱሳን መላእክትም በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ የተፈጠረው ሰው ከክብሩ ተዋርዶ ሲመለከቱ ተከዙ ፡፡
የሰው ልጅ ጠፍቶ እንዲቀር ያልወደደው እግዚአብሔር ወልድ ሰውን ለማዳን ራሱን ዝቅ አድርጎ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሱዋ ነፍስ ነስቶ ተወለደ ፡፡ቅዱሳን መላእክትም ከላይ ከአርያም ከአባቱ ሳይለይ እግዚአብሔር ወልድ ሰውን ለማዳን ሲል በግዕዘ ሕፃናት ተወልዶ ፣በእናቱም እቅፍ ሆኖ ፤ እንስሳት እስትንፋሳቸውን እያሟሟቁትበማየታቸው ተደነቁ ፡፡ሰውን ለማዳን ሲል ራሱን ዝቅ በማድረግ የባርያውን አርአያ እንደነሣ አስተውለው “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት፣ ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ”(ሉቃ.2፡14) ብለው አመሰገኑት ፡፡
ጌታችንም በመስቀሉ የማዳን ሥራውን ሲፈጽም ተጎሳቁሎ የነበረውን የሰው ባሕርይ ወደ ቀድሞ ክብሩ መለሰው፡፡ ስለዚህም እንደ ቅዱሳን መላእክት አምላኩን ለማመስገን እድሉን አገኘ ፡፡ (ዮሐ.4፡23) ነገር ግን ከእነርሱ ጋር በመሆን ሙሉ ለሙሉ በምስጋና የሚሳተፈው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሙታንስ በሚነሡበት ጊዜ በሰማያት እንደ እግዚአብሔር መልአክት ሆነው ይኖራሉ…….”(ማቴ.22፡30)እንዳለው በትንሣኤ ዘጉባኤ ነው ፡፡ እስከዚያ ድረስ ግን በዚህ ምድር ሳለን ከእኛ የሚጠበቅብንን ፣ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቃል ያስተማረንን፣ በሥራም ያሳየንን ተግባር ተግብረን፣ እንደ ቅዱሳን መላእክት ለአምላካችን በመንፈስና በእውነት በመሆን አምልኮታችንን እንድንፈጽም የእነርሱ ተራዳኢነት በእጅጉ ያስፈልገናል ፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ “መላእክት ሁሉ መናፍስት አይደሉም? የዘለዓለም ሕይወትን ይወርሱ ዘንድ ስለ አላቸው ሰዎችስ ለአገልግሎት ይላኩ የለምን?”(ዕብ.1፡14) ማለቱ ፡፡ “የዘለዓለም ሕይወትን ይወርሱ ዘንድ” የተባልነው ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌሉ “እነርሱ በእውነት ቅዱሳን ይሆኑ ዘንድ ስለእነርሱ ራሴን እቀድሳለሁ፡፡ የምለምንህም ስለ እነዚህ ብቻ አይደለም፤ በቃላቸው ስለሚያምኑብኝ ሁሉ ነው እንጂ”(ዮሐ.17፡19-20)እንዳለው በክርስቶስ አምነን ለተጠመቅነው ክርስቲያኖች ነው፡፡

እናት ልጁዋን እንድትንከባከብና እንድታገለግል ሁሉ ቅዱሳን መላእክትም የዘለዓለም ሕይወትን እንድንወርስ ይራዱናል፡፡ (ሉቃ.13፡6-9) ያለ እነርሱ እርዳታና ድጋፍ በቅድስና ሕይወት አድገን የመንግሥቱ ወራሾች መሆን አይቻለንም ፡፡ እንዲህም በመሆኑ በመንፈስ ቅዱስ የልጅነት ጸጋን ከማግኘታችን በተጨማሪ ቅዱሳን መላእክት እኛን ይራዱን ዘንድ ጠባቂ ተደርገው ተሰጥተውናል ፡፡ (ማቴ.18፡10)

ቅዱስ ጳውሎስ “እናንተ ግን የሕያው እግዚአብሔር ከተማ ወደምትሆን ወደ ጽዮን ተራራ በሰማያት ወደ አለችው ኢየሩሳሌም ደስ ብሎአቸው ወደሚኖሩ አእላፍ መላእክትም ደርሳችኋል”(ዕብ.12፡22) በማለት እንደተናገረው በክርስቶስ የማዳን ሥራ ከቅዱሳን መላእክት ጋር አንድ ቤተሰብ መሆንን አግኝተናል ፡፡ ስለዚህም ጉዞአችንን ጨርሰን ገድላችንን ፈጸመን ለክብር እንድንበቃ ይራዱናል ፡፡ በመሆኑም የእኛ ሕይወት በኃጢአት ውስጥ መገኘት ሲያሳዝናቸው ፣ በንስሐ ወደ አባታችን መመለሳችን ደግሞ በእጅጉ ያስደስታቸዋል፡፡(ሉቃ.15፡7) ስለዚህ ስለእኛ በቅድስና ሕይወት መဝይላል(1ጢሞ.5፡8)፡፡ እኛ የእነርሱ ቤተሰብ ሆነናልና ቤተሰባዊ ግዴታቸውን ለመወጣት ሲሉ ፣ ደካማው ብርቱን እንዲረዳ ቅዱሳን መላእክትም እኛን ለመርዳት ይተጋሉ፡፡ ነገር ግን የእነርሱ እርዳታ ለእኛ የሚፈጸምልን ተራዳኢነታቸውንና ምክራቸውን የተቀበልን እንደሆን ብቻ ነው ፡፡ ምክንያቱም እነርሱም እንደ አምላካቸው በእኛ ነጻ ፈቃድ ውስጥ ጣልቃ አይገቡምና ፡፡ እንዲህም ስለሆነ የሎጥ ሚስት ምንም እንኳ በመልአኩ እጅ ብትያዝም ለመልአኩ ቃል ባለመታዘዙዋና ለመዳን ባለመፍቀዱዋ የጨው ሐውልት ሆና ቀርታለች(ዘፍ.19፡26) ፡፡ በእርግጥ ቅዱስ ጳውሎስ “በመላእክት የተነገረው ቃል ጽኑ ከሆነ መተላለፍና አለመታዘዝ የጽድቅን ብድራት ከተቀበለ..”(ዕብ.2፡2) በማለት እንደገለጠልን እግዚአብሔር ለላከው መልአክ አለመታዘዝ ታላቅ የሆነ ቅጣትን ማምጣቱ የማይቀር ነው፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን ልጆቹዋ የመላእክትን ተራዳኢነት አውቀው እንዲጠቀሙና የመንግሥቱ ወራሾች ለመሆን እንዲበቁ ስትል ለቅዱሳን መላእክት የመታሰቢያ ቀን በመስጠት በእነርሱ የምናገኛቸውን እርዳታዎች እንዲታወሱ ታደርጋለች ፡፡

በዚህም መሠረት በህዳር ወር በዐሥራ ሁለተኛው ቀን ቤተ ክርስቲያናችን የታላቁ መልአክ የቅዱስ ሚካኤልን በዓለ ሲመት በታላቅ ድምቀት ታከብረዋለች ፡፡ እንደ ቅዱሳን አባቶቻችን አስተምህሮ ህዳር 12 ቀን ታላቁ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል በኢዮር ባለችው በአራተኛይቷ ከተማ በሚኖሩት ኃይላት እና በአሥሩ ነገደ መላእክት ላይ አለቃ ሆኖ የተሾመበት ቀን ነው ፡፡እግዚአብሔር ሳጥናኤልን በትዕቢቱ ምክንያት ከሥልጣኑ ገፍፎ ወደ ምድር ሲጥለው ቅዱስ ሚካኤል በእርሱ ቦታ በዐሥሩ ከተማ በመቶውም ነገደ መላእክት ላይ ተሹሟል፡፡(ይህን ሁለተኛውን ሹመት ያገኘው በሚያዚያ 2 እንደሆነ አክሲማሮስ በሚባለው የቤተክርስቲያናችን መጽሐፍ ላይ ሰፍሮ አናገኛለን፡፡)

የቅዱስ ሚካኤል ሹመት በነገደ መላእክት ላይ ብቻ ግን አይደለም ፤ ነገር ግን የእግዚአብሔር ሕዝብ በሆኑት ላይም ጭምር ነው ፡፡ ይህም እንደሆነ እንድንረዳ በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ሕዝብ የተባለውን እስራኤል ዘሥጋን ሲራዳና ሲጠብቅ እንደነበረ ተጽፎልን እናገኛለን ፡፡ ለምሳሌ መጽሐፍ ቅዱስ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ለኢያሱ በኢያሪኮ ምድረ በዳ እንደተገለጠለት “… ዐይኑን አንሥቶ ተመለከተ እነሆም የተመዘዘ ሰይፍ የያዘ ሰው በፊቱ ቆመ ፤ ኢያሱም ወደ እርሱ ቀርቦ “ከእኛ ወገን ወይስ ከጠላቶቻችን ወገን ነህ ? አለው ፡፡ እርሱም “እኔ የእግዚአብሔር ሠራዊት አለቃ ሆኜ አሁንም ወደ አንተ መጥቼአለሁ”(ኢያ.5፡13) ይለናል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ሕዝበ እስራኤልን ከግብጽ ባርነት ነፃ ሲያወጣቸው ይመራቸው የነበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ነበር ፡፡ ሹመቱ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይም በመሆኑ ስለ እነርሱ ዲያብሎስ ይዋጋው ፣ በጸሎትም ይራዳቸው ነበር ፡፡ ነገር ግን ኃጢአት ሠርተው ሲያገኛቸው ለእግዚአብሔር አድልቶ ኃጢአተኞችን ስለሚቀጣ እግዚአብሔር ሕዝቡን “በፊቱ ተጠንቀቁ ቃሉንም አድምጡ ስሜም በእርሱ ስለሆነ ኃጢአት ብትሠሩ ይቅር አይልምና አታስመርሩት”(ዘጸ.23፡21)ብሎ አስጠንቅቋቸው ነበር ፡፡ ይህም ቅዱስ ሚካኤል በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ መሾሙን ያስረዳናል ፡፡ ነገር ግን ከላይ የተጠቀሱት ጥቅሶች ሕዝበ እስራኤልን ይራዳቸው የነበረው ቅዱስ ሚካኤል ስለመሆኑ አያረጋግጥም የሚል ካለ “መልአክ” የተባለው ቅዱስ ሚካኤል ስለመሆኑ ቅዱስ ገብርኤል ወደ ነቢዩ ዳንኤል በተላከ ጊዜ ገልጦልን እናገኛለን፡- ቅዱስ ገብርኤል በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ቅዱስ ሚካኤል ስለመሾሙ ሲመሰክር “በእውነት በመጽሐፍ የተጻፈውን እነግርሃለሁ፤ በዚህም ነገር ከአለቃችሁ ከሚካኤል በቀር የሚረዳኝ ማንም የለም”(ዳን.10፡21)ብሎአል፡፡ ስለዚህም ለኢያሱ የተገለጠውና እስራኤላውያንንም የመራው መልአክ ቅዱስ ሚካኤል መሆኑን እንረዳለን ፡፡

የቅዱስ ሚካኤል አለቅነት በሐዲስ ኪዳንም አንደሚቀጥል ይህ ነቢይ በትንቢቱ “በዚያ ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ ሚካኤል ይነሣል..”(ዳን.12፡1) በማለት ተናግሮለታል ፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ሚካኤል እኛን ከሰይጣን አሽክላና ወጥመድ ይጠብቀንና በጸሎቱ በእግዚአብሔር ፊት ይቆምልን ዘንድ በእኛም ላይ ሹም ነው ፡፡ ምክንያቱም እኛ የእግዚአብሔር ሕዝቦችና የርስቱ ወራሾች ነንና፡፡

እግዚአብሔር ነቢዩ ሙሴን የሕዝቡ መሪ አድርጎ መሾሙ እጅግ ትሑትና ስለመንጎቹን ነፍሱን እንኳ አሳልፎ እስከመስጠት ደርሶ ስለሚወዳቸው ነበር፡፡(ዘኁል.12፡3፤ዘጸአ.32፡32) በሕዝቡም ላይ እርሱን መሾሙ እንዲሠለጥንባቸው ወይም እንዲገዛቸው ሳይሆን በትምህርቱና በጸሎቱ እነርሱን እንዲቤዣቸው ነው ፡፡ እንዲህም ስለሆነ ቅዱስ እስጢፋኖስ ስለሙሴ ሲመሰክር “እግዚአብሔር ሹምና ቤዛ አድርጎ ላከው”አለ፡፡ (የሐዋ.7፡35) እንዲሁ ቅዱስ ሚካኤል ነው ፡፡ ቅዱስ ሚካኤል እጅግ ትሑትና ለሠራዊቱ ተቆርቋሪ የሆነ መልአክ በመሆኑ በመላእክትና በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ተሾመ ፡፡ በመላእክትና በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ መሾሙ ልክ እንደ ሙሴ በእነርሱ ላይ ሊሠለጥንባቸው ወይም ሊገዛቸው ሳይሆን መላእክትን ሊመራ ፣ እኛን ደግሞ ከሰይጣን ጥቃት ሊጠብቀንና በጸሎቱ ሊራዳን ነው (ይሁዳ.12) ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቅዱሳን መላእክት እኛን እንደሚጠብቁና እንደሚራዱ እንዲሁም ስለእኛ በፊቱ አንደሚቆሙ ሲያስተምረን“ከእነዚህ ከታናናሾቹ አንዱን ስንኳ እንዳትንቁ ተጠንቀቁ፤ መላእክቶቻቸው በሰማያት ሁል ጊዜ በሰማይ ያለውን የአባቴን ፊት ያያሉ እላችኋለሁ”(ማቴ.18፡10) ብሎናል ፡፡ እኛን ይጠብቁ ዘንድ የተሰጡን ቅዱሳን መላእክት ስለእኛ እንዲህ የሚቆረቆሩና ስለመዳናችን የሚተጉ ከሆነ በቅድስናው ልቆ የመላእክት አለቃ ሆኖ የተሾመው ቅዱስ ሚካኤል እንዴት ስለእኛ በእግዚአብሔር ፊት ይበልጥ አይቆም?(ሉቃ.13፡6-9) እንዴትስ በተሰጠው ሥልጣንና ኃይል አይረዳን?(መዝ.33፡7) እርሱ “ስለሕዝብህ ልጆች የሚቆመው”መባሉም እኛን በጸሎቱና በተራዳኢነቱ የጽድቅ ሕይወታችንን በሚገባ እንድናከናውን እንደሚራዳን የሚያሳይ ኃይለ ቃል ነው ፡፡

የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤል ጸሎቱና በረከቱ በእኛ ላይ ለዘለዓለሙ ይደርብን አሜን ፡፡
ከማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ የተወሰደ

20111221

እንኳን ለአባታችን ኣባ ሳሙኤል የእረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ


እንኳን ለአባታችን ኣባ ሳሙኤል የእረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ አባታችን አባ ሳሙኤል ዘደብረ ዋሊ (ዋልድባ) የተባሉ ኢትዮጵያዊ ጻድቅ ኣባታቸው እስጢፋኖስ እናታቸው ዓመተ ማርያም ይባላሉ:: ትውልዳቸው አክሱም ሽሬ አካባቢ ተወለዱ በኋላም አባታቸውና እናታቸው ስለሞቱባቸው ወደ ገዳም ሄደው ገቡ በዚህም ጊዜ በመንፈሳዊ ትምህርታቸው ላቁ (ጎለመሱ) ተነስተውም ወደ ደብረ መንኮል ገዳም ገቡና ከአባ አድኃኒ ከተባሉ አባት መነኮሱ በዚህም ገዳም ኢይበልዕ ዘእንበለ ሐምል ይለዋል ከጎመን በስተቀር ሌላ ምግብ አይበሉም ነበርና ሲሰግዱም እግራቸው እስኪአብጥ ድረስ ይሰግዱ ነበር። በጾመ ፵ ጊዜም ፵ መአልትና ፵ ሌሊት ምንም ሳይቀምሱ ቆዩ በዚህም ጊዜ ብዙ አናብስት ተሰብስበው ወደ እሳቸው መጡና ግማሾቹም ለእሳቸው እንደፈረስ መሄጃ ግማሾቹም ለቅዱሳን መጻህፍትቶቻቸው መጫኛ እንዲሆኑ የረገጡትን መሬት እየላሱ እንዲኖሩ ታዘዙ። በዚህ ዓይነት ኑሮ ሲኖሩ ወደ ዋልድባ ገዳም ገብተው ገዳሙን አቀኑ መሰረቱ በዋልድባ ገዳም ሲጸልዩ ፳፬ቱ ካህናተ ሰማይ መንበሩን ሲያጥኑ ተገለጸላቸው ከዚህም ሌላ እሳቸው ቅዳሴ ገብተው ቅዳሴ ማርያምን ሲቀድሱም ሆነ ሲደግሙ ከመሬት አንድ ክንድ ከፍ ብለው መሬት ለቀው ይቆሙ ነበር ለእሳቸው ግን አይታወቃቸውም ነበር ከብቃታቸው ብዛት የተነሳ ሌላው ደግሞ ከፍቅራቸው ጽናት የተነሳ ቅዳሴዋንና ውዳሴዋን በቀን በቀን በእድሜዋ ልክ ፷፬ ጊዜ ሲደግሙ ከ፪ ክንድ በላይ ከመሬት ይለቁ ነበር ከሰማይ የወርቅ ጽዋ ወርዶላቸው የቀድሱበት ነበር አባ ሳሙኤል ዋልድባን እንደመሶብ በእጃቸው ይዘው አስባርከዋታል የበረከት ሀገር አንድትሆን ዛሬ በዋልድባ ረሐብ የለም ቅዳሴ ማርያም ሳይደግም የሚውል መነኩሴ የለም አባ ሳሙኤል በዋልድባ ሁነው አባ አንበሳ በአዘሎ ሁነው አባ ብንያም በግብጽ ሁነው ሲጸልዩ በመንፈስ ይተያዩ ነበርና ተቀጣጥረው ፫ቱም በአንበሳ ላይ ተቀምጠው ወደ ምድረ ከብድ ከአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ዘንድ በረከትን ለማግኘት ሄዱ።አባ ሳሙኤል ዘዋልድባ እረፍታቸው ታህሣስ፲፪ ቀን ነው ። የአባታችን ያባ ሳሙኤል አምላክ ይጠብቀን ረድኤት በርከታቸው በኛ በልጆቻቸው ላይ ይደርብን አሜን!!!

ታላቁ ፍጥጫ part1 በመምህር ምህረተአብ አሰፋ

ታላቁ ፍጥጫ part 2 በመምህር ምህረተ አብ አሰፋ

ሁለት ነገር ያስፈራኛል አንድ ነገር ያስተምረኛል በ መምህር ምህረተአብ አሰፋ

የአባ ዮሐንስ ኀፂር ሕይወት -ክፍል 1

ዮሐንስ ሐፂር

ዮሐንስ ሐፂር በላይኛው ግብጽ ቴባን በምትባል መንደር በ339 ዓ.ም ተወለደ፡፡ ወደ ገዳም አስቄጥስ የገባው በልጅነቱ ሲሆን ያን ጊዜ አበምኔቱ አባ ባሞይ ይባል ነበር፡፡ አባ ዮሐንስ በተመሥጦው እና በታዛዥነቱ የታወቀ አባት ነበር፡፡ በመጀመርያው የአስቄጥስ ጥፋት ጊዜ ገዳሙን ትቶ ወደ ቁልዝም ተጓዘ፡፡ ያረፈውም በዚያ ነው፡፡
የዮሐንስ ሐጺርን ትምህርቶች ከዚህ እንደሚከተለው አቅርበነዋል ፡፡

1. የጠላቱን ከተማ ለመቆጣጠር የዘመተ ንጉሥ አስቀድሞ የውኃውን መንገድ ይዘጋል፣ የእህሉንም መግቢያ ይይዛል፡፡ ያን ጊዜ ጠላቶቹ ይራባሉ፣ ይጠማሉ፡፡ በመጨረሻም እጃቸውን ይሰጣሉ፡፡ የነፍስን ፆር ለማሸነፍም በተመሳሳይ መንገድ መጠቀም ይገባል፡፡ አንድ ሰው በጾምና በረኃብ ከጸና የነፍሱ ጠላቶች ይዳከማሉ፡፡

2. እኔ በትልቅ ዋርካ ሥር የተቀመጠንና አራዊት ሊጣሉት የመጣን ሰው እመስላለሁ፡፡ ሊቋቋማቸው እንደማይችል ከተረዳ ሸሽቶ ወደ ዛፉ በመውጣት ነፍሱን ያድናል፡፡ በእኔም የተፈጸመው ይኼው ነው፡፡ በበዓቴ ተቀምጬ ክፉ ሃሳቦች ሊቃወሙኝ ሲመጡ፣ ልቋቋማቸው እንደማልችል ባወቅኩ ጊዜ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ሸሽቼ እመሽጋለሁ፡፡ በዚያም ከጠላቶቼ ፍላፃ እድናለሁ፡፡

ዮሐንስ ሐፂር
3. መለወጥ የምትፈልግን ነፍስ በተመለከተ አባ ዮሐንስ እንዲህ አለ፡- በአንዲት ከተማ ውስጥ ብዙ ወዳጆች የነበሯት አንዲት አመንዝራ ሴት ነበረች፡፡ ከገዥዎቹ አንዱ ቀረባትና ‹መልካም ሴት ለመሆን ቃል ግቢልኝና አገባሻለሁ› አላት፡፡ እርሷም ቃል ገባችለትና ተጋቡ፡፡ ወደ ቤቱም ወሰዳት፡፡ የቀድሞ አፍቃሪዎቿ ያቺን ሴት ፈለጓት፣ እርስ በርሳቸውም ‹ያ ልዑል ወደ ቤቱ ወስዷታል፤ ወደ ቤቱ ብንሄድ ይቀጣናል፡፡ ነገር ግን በጓሮ በኩል እንሂድ፣ ለርሷም እናፏጭላት፣ የፉጨቱን ድምፅ ስትሰማ ከድርሱ ወርዳ ወደኛ ትመጣለች፣በዚህም ያለ ችግር እናገኛታለን› ተባባሉ፡፡ ወደ ቤቷም ጓሮ ተጉዘው ያፏጩ ጀመር፡፡ እርሷ ግን የፉጨቱን ድምፅ ስትሰማ ጆሮዎቿን ደፈነች፡፡ ወደ ውስጣዊው እልፍኝም ገባች፡፡ በሩንም ጥርቅም አድርጋ ዘጋች፡፡ ይህቺ ሴት የኛ ነፍስ ምሳሌ ናት፡፡ ወዳጆቿ የተባሉም ፈተናዎቿ ናቸው፤ ገዥ የተባለውም ክርስቶስ ነው፣ እልፍኝ የተባለውም ዘለዓለማዊው ቤት ነው፡፡ እነዚያ የሚያፏጩት ክፉዎች አጋንንት ናቸው፤ ነገር ግን ነፍስ ሁልጊዝም በክርስቶስ አምባነት ትሸሸጋዋለች፡፡

4. አባ ዮሐንስ ልቡናው ከእግዚአብሔር ጋር ስለነበረ ምድራዊ ነገሮችን ይዘነጋ ነበር፡፡ አንድ ቀን አንድ ወንድም ቅርጫት ሊወስድ ወደ አባ ዮሐንስ በኣት መጣ፡፡ አባ ዮሐንስም ምን ፈልጐ እንደሆነ ጠየቀው፡፡ ያም ወንድም ‹ቅርጫት ፈልጌ ነው› አለው፡፡ አባ ዮሐንስ ወደ በኣቱ ተመለሰና ዘንግቶት ወደ ሽመና ሥራው አመራ፡፡ ጥቂት ቆይቶ ያ ወንድም አንኳኳ፣ አባ ዮሐንስም ወጥቶ ‹ምን ፈልገህ ነው› አለው ‹ቅርጫት ስጠኝ ብየህ ነበር› ሲል መለሰለት፡፡ ተመልሶ ወደ በኣቱ ሲገባ ልቡናው በሰማያዊ ነገር ስለተመሰጠ ዘንግቶት ወደ ሽመናው ሥራ እንደገና ገባ፡፡ ለሦስተኛ ጊዜ ያ ወንድም ሲያንኳኳ አባ ዮሐንስ ተመልሶ ወጣና ‹ምን ፈልገህ ነው?› አለው፡፡ ‹ቅርጫት ስጠኝ ብየህ ነበር› አለና መለሰለት፡፡ አባ ዮሐንስም እጁን ይዞ እየጐተተ ወደ በኣቱ አስገባውና ‹ቅርጫት ከፈለግህ ያዝና ሂድ፣ በእውነቱ እንዲህ ላሉት ነገሮች እኔ ጊዜ የለኝም› አለው፡፡

5. አንድ ቀን አንድ ሰው ወደ አባ ዮሐንስ ሐፂር በኣት መጣና ሥራውን እያየ ያመሰግነው ጀምር፡፡ አባ ዮሐንስ ዝም አለውና ገመድ መሥራቱን ቀጠለ፡፡ እንግዳውም እንደገና ወሬውን ቀጠለ፣ አባ ዮሐንስም ጸጥ አለው፡፡ ለሦስተኛ ጊዜ እንግዳው ወሬ ሲያበዛ፡፡ ‹አንተ ወደ በኣቴ በመግባትህ እግዚአብሔር ወጥቶ ሄደ› ብሎ ተናገረው፡፡

6. አባ ዮሐንስ እንዲህ አለ፡- ‹የብሕትውናን ኑሮ በከተማ ውስጥ የሚኖር አንድ ሽማግሌ ነበረ፡፡ ያ ሰው በከተማው ውስጥ ከፍተኛ ቦታ የሚሰጠውና ባለዝናም ነበር፡፡ አንድ አረጋዊ አባት ከማረፉ በፊት ያንን ሰው ሊያየው እንደሚፈልግ ለዚያ ሰው ጥሪ ደረሰው፡፡ ያም ሰው በቀን ከተጓዝኩ ሰዎች ስለሚከተሉኝ ለኔ የተለየ ክብር ይሰጡኛል ብሎ አሰበ፡፡ ስለዚህም በሌሊት ሰው ሳያየው ለመጓዝ ወሰነ፡፡ በመሸ ጊዜም አሁን ማንም አያየኝም ብሎ ተነሣና ጉዞ ጀመረ፡፡ ነገር ግን ሁለት መላእክት ታዝዘው መብራተ ይዘው መንገዱን ይመሩት ነበር፡፡ ይህንን የተመለከቱ የከተማው ሰዎች ወደ እርሱ ተሰባሰቡ፣ መላ ከተማው ያንን የመላእክት ብርሃን እያየ ከኋላ ተከተለው፡፡ ከክብር በሸሸ ቁጥር የበለጠ ክብርን አገኘ፡፡ በዚህም ‹ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳል፣ ራሱንም የሚያዋርድ ሁሉ ከፍ ከፍ ይላል› የሚለው የወንጌል ቃል ተፈጸመ፡፡ (ሉቃ. 14.11)

7. አባ ጴሜን አባ ዮሐንስ እንዲህ ብሎ መናገሩን ገልጧል ‹ቅዱሳን በአንድ ቦታ የበቀሉ ዛፎችን ይመስላሉ፡፡ ከአንድ ምንጭ ጠጥተው፣ ልዩ ልዩ ዓይነት ፍሬ ያፈራሉ፡፡ የአንድ ቅዱስ ሥራ ከሌላው ይለያል፣ ነገር ግን በሁሉም አድሮ የሚሠራው አንድ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡
ዲያቆን መልአኩ እዘዘው የኔነህ

የቅዱሳን በረከት ይደርብን

ሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ



ከቅዱሳን
ሰማዕታት አንዱ የሆነው ማር ሚና 4ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ተጋድሎውን የፈፀመ ግብፃዊ ሰማዕት ሲሆን ህዳር 15 ቀን የሚነበበው ስንክሳር ቅዱስ ሚናስ በሚል ስያሜ ይገልፀዋል። በሶሪያ ቋንቋ ማር የሚለው ቃልቅዱስየሚልትርጉም ሲኖረው ለወንድ የሚሰጥ ቅጥያ ሲሆን ለሴት ደግሞ ማርታ ይሆናል ይሄውም ቅድስት ማለት ነው።
ቅዱስ ሚናስ ከእናቱ ከአውፌምያ እና ከአባቱ ከአውዶስዮስ ልዩ ስሙ ኒቆስ ሻቲ በተባለ መንደር 276 ተወለደ። እናቱ አውፌምያ ልጅ መውለድ ባለመቻሏ ታዝንና ትጨነቅ ነበር። ወደ ቤተ-ክርስቲያን ስትሄድም እናቶች ልጆቻቸውን ሲያቆርቡ ስታይ በማልቀስ ፈጣሪዋን ልጅ እንዲሰጣት ትለምን ነበር። እግዚአብሔርም የልመናዋን ቃል ሰምቶ ወንድ ልጅ ሰጣት።
አባቱ አውዶስዮስ የናይል ዴልታ አስተዳዳሪ የነበረ ሲሆን ለህዝቡ ባለው ፍቅርና ሐዘኔታ እንዲሁም በትክክለኛ ፍርድ ሰጭነቱ በአካባቢው ሰው ተወዳጅነትን ያተረፈ ሰው ነበር። አውፌምያም እግዚአብሔርን የምትፈራና ባለቤቷ በሚፈፅማቸው ቀና ምግባሮች ሁሉ ከጎኑ ሆና የምትደግፈውና የምታበረታታው ሴት ነበረች።
ቅዱስ ሚናስ ወላጆቹን ያጣው በልጅነት ጊዜው ሲሆን ከወላጆቹ የወረሰውንም ሃብትና ንብረት በመሸጥና ለድሆች በማከፋፈል እርሱ ግን ይህችን አለም ንቆ መነነ። በዘመኑ በነበሩ ጣዖት አምላኪ ነገስታት ተይዞ ለጣዖት አልሰግድም በማለቱ አንገቱን በሰይፍ ተቀልቶ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጀ ይህም የሆነው 24 ዓመቱ ነው።
ማር ሚና (ቅዱስ ሚናስ) በኢትዮጵያ ብዙም ባይታወቅም በጣና ቂርቆስ ከሰማዕቱ ከቅዱስ ቂርቆስና ከቅዱስ እስጢፋኖስ ጋር መቅደስ ታንፆለት እንደነበር
"ጠቢበ ጠቢባን ቂርቆስ ወእማዕምራን ማዕምር
ሐውፃ ለመቅደስከ እንተ ተሃንፀት በባህር፡
ምስለ እስጢፋኖስ ሰማዕት ወሚናስ ፍቁር።" የሚለው የመልክዐ ቂርቆስ ንባብ ምስክር ነው። የጠቢባን ጠቢብ የአዋቂዎች አዋቂ የምትሆን ቂርቆስ ሆይ ከሰማዕቱ እስጢፋኖስና ከተወዳጁ ከሚናስ ጋር በባህር ላይ የታነፀች መቅደስህን ጎብኛት ማለት ነው። እዚሁ መልክዕ ውስጥ በግብፅ በታወቀው የስም አጠራሩ "ሚና" በማለት የሚጠራውን ንባብ እናገኛለን።
"ሰላም ዕብል ዘምስለ ካልዕከ ሚና
ቂርቆስ ሕፃን ዘእያብፅሕኮ ውርዝውና" ለጉልምስና ያልበቃህ ሕፃን ቂርቆስ ሆይ ከጓደኛህ ከሚና ጋር ሰላም እልሃለሁ (ሰላምታ ላንተ ይሁን) ማለት ነው።በማለት በካይሮ አባስያ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን ቅድስት ማርያም //ቤት የተዘጋጀው የሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ እና የፓትርያሪክ ቄርሎስ ፮ኛ የህይወት ታሪክ በሚል የተዘጋጀው መፅሃፍ ይገልጻል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ስለሚገኘው ብቸኛው የቅዱስ ሚናስ ቤተ-ክርሰቲያን ምን ያህል ያውቃሉ?
የቅዱስ ሚናስ ቤተ-ክርሰቲያን ከባህር ዳር ከተማ በግምት 23 ርቀት ላይ በምዕራብ ጎጃም እና በደቡብ ጎንደር መሀከል ወይም በደራ ክፍለሃገር ከአቡነ ሐራ ድንግል ገዳም በግምት 3-4 ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን አካባቢውም በተለምዶ ሚናስ እየተባለ ይጠራል።
ቤተ-ክርስቲያኑ የተተከለበት ዘመን በውል ባይታወቅም ቤተክርስቲያኑ ግን በአፄ ፋስል ዘመነ መንግስት እንደነበር ገድለ አቡነ ሐራ ድንግል ያስረዳል።
በአፄ ሱስንዮስ ዘመነ መንግስት 1597 በነበረው የሐይማኖት መፋለስ ቅዱሳን በሃይማኖታቸው ሲሰደዱ ብዙ እንግልት መከራ እና ስቃይ ሲደርስባቸው በነበረበት በዚያ ዘመን የንጉሱ ግብረ አበሮች እና አድርባዮች ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን ሲመዘበሩና በእሳት ሲያቃጥሉ ይህን ቤተ-ክርስቲያን ግን ለማቃጠል ቢሞክሩም በእግዚአብሔር ተዓምር የቤተክርስቲያኑን በር መክፈትም ሆነ ቤተ-ክርስቲያኑን ማቃጠል አልተቻላቸውም ነበር። ከዚያን ጊዜ በኋላም ለማንም ሊከፈት ባለመቻሉ 17 ዓመት ተዘግቶ እንደቆየ አባቶች ይናገራሉ።
ገድለ አቡነ ሐራ ድንግልም የሃይማኖት መፍለስም ከሆነ 16 ዓመት በኋላ በአፄ ፋሲለደስ ንጉስ ትዕዛዝ ሃይማኖት እንደቀድሞዋ ሆነች የሮም ሃይማኖትም ፈለሰች በማለት ያስረዳል።
ከዚህ ሁሉ በኋላ አባታችን አቡነ ሐራ ድንግልም ወደ እርሳቸው ከመጡ መነኮሳት ጋር ተሰብስበው ወደ ቅዱስ ሚናስ ቤተ-ክርስቲያን ሄደው በመፀለይ 17 ዓመት ተዘግቶ የነበረ ቤተ-ክርስቲያን ተከፈተላቸው። በአንድነትም ቆሙ በማህሌትና በእልልታ በከበሮና በጸናጽንም አመስግነው የጌታችንና የመድሓኒታችንን ቅዱስ ስጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለው ወደ በዓታቸው እንደተመለሱ ገድለ አቡነ ሐራ ድንግል ይናገራል።
ቅዱሱ አባታችን አቡነ ሐራ ድንግል ከአረፉ በኋላ ግን ይህ ቤተክርስቲያን ሰው በማጣት ጠፍ የአራዊት መኖሪያ ሆኖ 400 ዓመት እንደቆየ አባቶች ይናገራሉ። ምንም እንኳን ይህ ቦታ የአራዊት መኖሪያ ቢሆንም ቅዱሳን ግን እንዳልተለዩት የአካባቢው ነዋሪዎችና የቀደሙ አባቶች ይናገራሉ። የቤተክርስቲያን ደወል እና የእጣን መዓዛ ይሸታቸው እንደነበርም ይመሰክራሉ።
የእግዚአብሔር ፈቃድ ሆኖ ከዛሬ ስድስት ዓመት በፊት በአቡነ ሐራ ድንግል ገዳም እገዛ እና በአካባቢው ነዋሪዎች ትብብር ዛሬ ያለው መቃረቢያ (መቃኞ) ተሰርቶ ታቦቱ ለመግባት ችሏል። በአሁኑ ሰዓት ደግሞ ባህርዳር ከተማ በሚገኘው የሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ የፅዋ ማህበር አማካኝነት ህንፃ ቤተ-ክርስቲያኑ በመገንባት ላይ ይገኛል።
የቅዱስ ሚናስ ዓመታዊ በዓሉ ህዳር ፲፭ ቀን በድምቀት ይከበራል። በሌላ ጊዜ ስለቤተክርስቲያኑ ታሪክ በሰፊው እንመለስበታለን
የሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ በረከት እና ረድኤት አይለየን
ከጽዮን አያሌው የፌስቡክ ገጽ የተወሰደ