20101006

እንኳን ለዘመነ ጽጌ በስላም አደረስን

ጌታ ሲወለድ ሰብአ ሰገል «የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ? በምሥራቅ ኮከቡን አይተን ልንስግድለት መጥተናል» እያሉ በኮከብ እየተመሩ በመጡ ጊዜ በይሁዳ በገሊላና በሰማርያ የሮማውያን ተወካይ የነበረው ንጉሥ ሄሮድስ የጌታችን ንግሥና ምድራዊ ንግሥና መስሎት መንግስቴን ሊቀማኝ ነው ብሎ ደነገጠ፡፡ ፊሪሳውያን «መሲህ ተወልዶ ከሮማውያን አገዛዝ ነጻ ያወጣናል፡፡» ብለው ያምኑ እንደነበር ስለሚያውቅም ይህ የተፈጸመ መስሎት ጭንቀቱ በረታ፡፡ የተወለደውን ሕፃንም ለመግደል ተነሳ፡፡
ስለዚህም ሰብአ ሰገልን አስጠርቶ «ሂዱ ሕፃኑን ፈልጉ ፤ ባገኛችሁትም ጊዜ እኔም እንድሰግድለት ወደ
እኔ ተመልሳችሁ ያለበትን ንገሩኝ» በማለት በሽንገላ ተናገራቸው፡፡
ጠቢባኑም ከሄሮድስ ከተለዩ በኋላ በኮከቡ እየተመሩ ጉዞአቸውን ቀጥለው ጌታችንን ከእናቱ ጋር አገኙት ፤ ተንበርክከው ሰገዱለት፤ ወርቅ ፣ ዕጣን፣ ከርቤ እጅ መንሻ አቀረቡለት፡፡
የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ሄሮድስ እንዳይመለሱ ነገር ግን መንገድ ቀይረው ወደ ሀገራቸው እንዲሄዱ በነገራቸው መሠረት በሌላ መንገድ ወደ መጡበት ተደብቀው ተመለሱ፡፡
«እነርሱም ከሄዱ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ «ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነስ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሸ እስክነግርህም በዚያ ተቀመጥ አለው፡፡ » /ማቴ. 2 13 14/.......ዮሴፍም ተነሣ በዕድሜዋ በጣም ልጅ የነበረችው እመቤታችን ገና የተወለደውን ሕፃን አቅፋ የምትቀመጥበት አህያም ተዘጋጀ፡፡
ጉዞአቸውን ጀመሩ........
በቤተክርስቲያን አስተምህሮ ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 6 ዘመነ ጽጌ ወርኃ ጽጌ ይባላል:: ይኸውም ተራሮችን ሸንተረሮችን በአበባ ያስጌጠ ሰማይን በከዋክብት ያጌጠ ምድርን በስነ ጽጌያት ያሸበረቀ አምላክ ነው እና:: እሱ የሚመሰገንበት ስለሆነ .....ሌላው ጽጌ የተባለች እናቱ ድንግል ማርያም ፍሬ የተባለ ልጇ እሱን ኢየሱስ ክርስቶስን አዝላ ከኢየሩሳሌም ምድረ እስራኤል ወደ ግብጽ እንዲሁም ወደ አገራችን ኢትዮጵያ የተሰደደችበትን በማሰብ ለአርባ ቀናት ያህል ምዕመናን በፈቃዳቸው ለበረከት ይፆማሉ:: ሊቃውንቱም ከምሽቱ ሶስት ሰዓት እስከ ንጋቱ አስራ ሁለት ሰዓት ድረስ «ጽጌ ጽጌ ዘሰሎሞን ወዳዊት ጽጌ አሮን ዘክህነት» እያሉ ያመሰግኗታል:: እመቤታችንም በስደቷ ወራት ብዙ መከራ ደርሶባታል ተርባለች ተጠምታለች ልጄን ይገሉብኛል ብላ ተጨንቃለች::
ጌታ ወደ ግብጽ የተሰደደው ለምንድን ነው ቢሉ?....
(አንደኛ)..ነቢዩ ኢሳያስ የተናገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ነው:: «ወይወርድ እግዚእነ ተጽእኖ ድበ ደመና ቀሊል» «ጌታችን በፈጣን ደመና ሆኖ ወደ ግብጽ ይወርዳል» ኢሳያስ 19 ቁ. 1
(ሁለተኛ).. በግብጽ አምልኮተ ጣኦት ብዝቶ ነበር እና አምልኮተ ጣኦትን ለማጥፋት ነው::
እመቤታችን ሶስት አመት ከስድስት ወር እስኪፈጸም ድረስ በብግጽ እናም በሀገራችን በኢትዮጵያ የስደት ጊዜ አሳልፋለች ማቴ..2 ቁ. 19
በስደት ከቆዩ በኋላ ሄሮድስ ሞተ።.....ሄሮድስም ከሞተ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በግብጽ ለዮሴፍ በሕልም ታይቶ «የሕፃኑን ነፍስ የፈለጉት ሞተዋልና ተነሣ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ አለው፡፡ እርሱም ተነስቶ ሕጻኑንና እናቱን ይዞ ወደ እስራኤል ሀገር ገባ» ማቴ 2-19-21/
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከመስከረም 26 ቀን ጀምሮ እስከ ኅዳር 6
ቀን ድረስ የጌታን እና የእመቤታችንን ስደት በማሰብ የጽጌ ፆም ይፆማል
እንኳን አደረሳችሁ!!!

1 comment: